www.maledatimes.com አላሙዲ በኦሮሚያ ክልል የተገኘው ከፍተኛ ክምችት ያለው የወርቅ ማዕድንን ሊያወጡ ነው። - MALEDA TIMES
Loading...
You are here:  Home  >  Ethiopia  >  Current Article

አላሙዲ በኦሮሚያ ክልል የተገኘው ከፍተኛ ክምችት ያለው የወርቅ ማዕድንን ሊያወጡ ነው።

By   /   May 10, 2015  /   Comments Off on አላሙዲ በኦሮሚያ ክልል የተገኘው ከፍተኛ ክምችት ያለው የወርቅ ማዕድንን ሊያወጡ ነው።

    Print       Email
0 0
Read Time:2 Minute, 30 Second
ምንጭ  ሪፖርተር ጋዜጣ

ብሔራዊ ማዕድን ኮርፖሬሽን በኦሮሚያ ክልል ጉጂ ዞን ዳዋ ዲጋቲ ቀበሌ በሚገኘውና በልዩ መጠሪያው ኦኮቴ ተብሎ በሚጠራው ሥፍራ ያገኘው ከፍተኛ ክምችት ያለው የወርቅ ማዕድን ላይ ሥራ ሊጀምር መሆኑን፣ የኮርፖሬሽኑ ባለቤትና ባለሀብት ሼክ መሐመድ ሁሴን ዓሊ አል አሙዲ ሚያዝያ 29 ቀን 2007 ዓ.ም. ገለጹ፡፡

ሼክ አል አሙዲ ከፍተኛ የወርቅ ክምችት መገኘቱን የገለጹት፣ ሚድሮክ ቴክኖሎጂ ግሩፕ በማዕድንና በአግሮ ፕሮሰሲንግ ዘርፍ የስምንት ቢሊዮን ብር ማስፋፊያ ፕሮጀክት መጀመሩን አስመልክቶ በሸራተን አዲስ ጋዜጣዊ መግለጫ ሲሰጡ ነው፡፡

ብሔራዊ ማዕድን ኮርፖሬሽን ላለፉት 15 ዓመታት ባደረገው ጥናት የወርቅ ክምችቱ መገኘቱን የተናገሩት ባለሀብቱ፣ ‹‹የማዕድን ሥራችን እየሰፋ ነው፡፡ ቦታው ትልቅ የወርቅ ልማት ያለበት ነው፡፡ ትልቅ የወርቅ ክምችትም አግኝተናል፡፡ ለሚድሮክ ጎልድ ትልቅ ፕሮጀክት ከመሆኑም በተጨማሪ ኢትዮጵያን የሚያስጠራ ፕሮጀክት ነው፤›› ብለዋል፡፡

የተገኘው የወርቅ ክምችት ለሚቀጥሉት 15 ዓመታት ከ20 ቢሊዮን ዶላር በላይ ለአገሪቱ ገቢ የሚያስገኝ መሆኑን ጠቁመው፣ ሁሉም ዝርዝር ጥናት እየተጠናቀቀ በመሆኑ፣ በቅርቡ ወደ ሥራ እንደሚገባም ሼክ አል አሙዲ ገልጸዋል፡፡ ሌላው በትግራይ ክልል ስለተገኘው የማዕድን ክምችት ገልጸው፣ ብዙ ወርቅ ባይኖርበትም የዚንክ፣ የሊድና የብር ክምችት መገኘቱንና ወደ ምርት ለመግባት ዝግጅት እየተደረገ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ የሶዳ አሽ ፕሮጀክት እንዳላቸውና ማምረት መጀመራቸውንም አክለዋል፡፡

በሌላ በኩል በዶ/ር አረጋ ይርዳው ዋና ሥራ አስፈጻሚነት የሚመራው ሚድሮክ ቴክኖሎጂ ግሩፕ ወደ ላቀ ስኬት የሚያሸጋግረውን አዲስ ፕላን መንደፉን ገልጾ፣ የወርቅ ማዕድንና አግሮ ፕሮሰሲንግ ማስፋፊያ የስምንት ቢሊዮን ብር ፕሮጀክት ይፋ አድርጓል፡፡

ዋና ሥራ አስፈጻሚው ዶ/ር አረጋ እ.ኤ.አ ከ2015 ጀምሮ ቴክኖሎጂ ግሩፑ ተግባራዊ ማድረግ የሚጀምረው ዕቅድ ከ15 እስከ 20 ዓመታት የሚያገለግል መሆኑን ተናግረዋል፡፡ በስምንት ቢሊዮን ብር ወጪ የሚስፋፉት ፕሮጀክቶች የወርቅ ማዕድን ልማት፣ የተቀናጀ ዘመናዊ የዶሮ ዕርባታ፣ በመስኖ የተደገፈ ዘመናዊ የከብት መኖ (አልፋ አልፋ) ልማትና የተቀናጀ የወተትና የሥጋ ልማትን እንደሚያካትቱ አስረድተዋል፡፡

የማስፋፊያ ፕሮጀክቶቹ በሦስት ክልሎች እንደሚከናወኑ የገለጹት ዋና ሥራ አስፈጻሚው፣ 4.2 ቢሊዮን ብር (55 በመቶ የሚሆነው) በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል የማዕድን ሥራ፣ ቀሪው በአማራ ክልል ለሚካሄደው አግሮ ፕሮስሲንግ (የዶሮ እርባታ) እና በኦሮሚያ ክልል ለሚካሄደው አግሮ ፕሮሰሲንግ (የመኖ፣ የወተትና የሥጋ) ማስፋፊያ ፕሮጀክቶች የሚውል መሆኑን አስረድተዋል፡፡ የማስፋፊያ ፕሮጀክቱን ለማጠናቀቅ ከሦስት እስከ አምስት ዓመታት የሚወስድ መሆኑንም አስታውቀዋል፡፡

በማዕድንና በአግሮ ፕሮሰሲንግ የሚደረገው ኢንቨስትመንት ሥራው ተጠናቆ ሙሉ በሙሉ ወደ ሥራው ሲገባ፣ በየዓመቱ ከምርት ሽያጭ 3.5 ቢሊዮን ብር ገቢ እንደሚገኝና በልማቱ ዕቅድ ዘመን 61. 90 ቢሊዮን ብር የሽያጭ ገቢ ሊገኝ እንደሚችል ዕምነታቸው መሆኑን ዶ/ር አረጋ ተናግረዋል፡፡ ከልማቱ በታክስ፣ በሮያሊቲና በሌሎች ክፍያዎች በየዓመቱ 880 ሚሊዮን ብር ለመንግሥት ገቢ እንደሚደረግ ገልጸው፣ በተወጠነው የኦፕሬሽን የዕቅድ ዘመን (ከ15 እስከ 20 ዓመታት) በጠቅላላው 14.85 ቢሊዮን ብር የሚደርስ ገቢ ሊሰበሰብ እንደሚቻል አስረድተዋል፡፡ ቴክኖሎጂ ግሩፑ ቅድሚያ የሚሰጣቸው የልማት ዘርፎች የወርቅ ማዕድንና አግሮ ፕሮስሲንግ መሆናቸውን የጠቆሙት ዶ/ር አረጋ፣ ማዕድንን በሚመለከት ዋናው ተዋናይ ሚድሮክ ወርቅ ኩባንያ መሆኑንና አግሮ ፕሮስሲንጉን በሚመለከት ደግሞ ኤልፎራ አግሮ ኢንዱስትሪ መሆኑን ጠቁመዋል፡፡

ሚድሮክ ወርቅ በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ባለፉት አሥር ዓመታት በመተከል አካባቢ ሰፊ የማዕድን ፍለጋ ሲያካሂድ ቆይቶ፣ በቂ የወርቅ ክምችት መኖሩን ካረጋገጠ በኋላ ባህር ዶልቢር ሚኒራልስ ኢንዱስትሪ አድቫይዘርስ በተባለ የእንግሊዝ ኩባንያ የአዋጭነት ጥናቱን ማስጠናቱን ዋና ሥራ አስፈጻሚው ገልጸዋል፡፡ አሥር ዓመታት የፈጀውን የማዕድን ፍለጋ ግን ኢትዮጵያውያን የኩባንያው ሠራተኞች ማከናወናቸውን አክለዋል፡፡ ኩባንያው በለገደንቢ፣ በሳካሮ፣ በሻኪሶና በረጂ ከተሞች አካባቢ የወርቅ ማምረቻ እንዳሉት ይታወቃል፡፡ ለአሥር ዓመታት ባደረገው የማዕድን ፍለጋ 310 ሚሊዮን ብር ወጪ ማድረጉንም ዶ/ር አረጋ አክለዋል፡፡ ሚድሮክ ጎልድ በመተከል አካባቢ ያገኘውን የወርቅ ማዕድን ልማት በ200 ሚሊዮን ዶላር ወይም 4.2 ቢሊዮን ብር ወጪ እ.ኤ.አ. በ2015 እንደሚጀምርም ጠቁመዋል፡፡

 

Happy
Happy
0 %
Sad
Sad
0 %
Excited
Excited
0 %
Sleepy
Sleepy
0 %
Angry
Angry
0 %
Surprise
Surprise
0 %
    Print       Email
  • Published: 9 years ago on May 10, 2015
  • By:
  • Last Modified: May 10, 2015 @ 11:08 am
  • Filed Under: Ethiopia

Average Rating

5 Star
0%
4 Star
0%
3 Star
0%
2 Star
0%
1 Star
0%
<"Without the support of our readers, the Maleda Times website would not exist in its present form">

You might also like...

በሰሜን ሸዋ ዞን ኤፍራታ እና ግድም ወረዳ መከላከያ ከአማራው ማህበረሰብ እና ከፋኖ ጋር ጦርነት ገጥሟል

Read More →

This site is protected by wp-copyrightpro.com

%d bloggers like this:
Skip to toolbar