www.maledatimes.com ” የየጁ ደብተራ…” በኤርሚያስ ለገሰ - MALEDA TIMES
Loading...
You are here:  Home  >  Ethiopia  >  Current Article

” የየጁ ደብተራ…” በኤርሚያስ ለገሰ

By   /   November 21, 2015  /   Comments Off on ” የየጁ ደብተራ…” በኤርሚያስ ለገሰ

    Print       Email
0 0
Read Time:3 Minute, 13 Second

 

ከቅርብ አመታት ወዲህ በአከባበር እየተለወጠ የመጣውን የህውሀት እና ልጆቹን ልደት አጨንቁሮ ለተመለከተ ብዙ ነገሮችን መናገር ይችላል። በልሙጡ ለሚያይ ሰው የብአዴን፣ ኦህዴድ እና ደኢህዴግ የልደት በአላት ” መወድሰ ህወሀት” እየሆኑ መሔዳቸውን በቀላሉ መታዘብ ይችላል። ህውሀቶች የየካቲት 11 እና እሱን ተከትሎ የነበሩት ሳምንታት አልበቃቸው ብሎ ህዳር 11 ( የኦህዴድ እና የሐይለማርያምን ልደት ቀን ረሳሁት) በቤቢ ሻወርነት እየተጠቀሙበት ነው። ርግጥ ነው ህውሀቶች ወገባቸውን ይዘው ” እኛ በልጆቻችን ውስጥ አድረን ቡራኬያችንን ብንወስድ እናንተን ለምን አሳከካችሁ?” እንደሚሉን ይገባኛል። ባያሳክከን ጥሩ ነበር። ፈር የሳተው ቡራኬ በኢትዬጲያ ህዝብ ላይ እያሳረፈ ያለው ጫና በአይናችን ላይ እየሔደ አላሳከከንም ማለት እንደ ብአዴን አባላት ቧልት ስለሚሆንብን ነው። እናም ቢያንስ የብአዴን አባላትን የውስጥ ጩኸት እኛ ብንጮኸው ምስጋናቸው ዘግይቶም ይደርሰን ይሆናል።

1• ” ከማን አንሼ!”

ብአዴን በዘንድሮው ልደቱ የማንነት ቀውስ በፈጠረው ምክንያት ያልሆነውን ሆኖ መታየት ፈልጓል። ያልሆኑትን ሆኖ የመታየት ጉጉት የመነጨው በተለያየ ምክንያት ሊሆን ይችላል። የመጀመሪያው ምክንያት ባለፈው የካቲት ህውሀት የተመሰረተበት በአል ከደደቢት (መቀሌ) እስከ ሞያሌ፣ ከጐሬ እስከ ደወሌ፣ ከሞቃዲሾ እስከ ሎስ አንጀለስ በደመቀ ሁኔታ ተከብሮ ነበር። በልደት በአሉ በኢትዬጲያ ምድር ታይተው የማይታወቁ አንፀባራቂ ገድሎች ተደምጠዋል። የህውሀትን ታላቅነት የሚያስተጋቡ ውዳሴዎች ተሰምተዋል። ለህዝብ የሚቀርብ እዚህ ግባ የሚባል ሀሳብ ማመንጨት የተሳነው ህውሀት አልፋ እና ኦሜጋውን ያለፋት መንግስታት ሲረግምና ሲያወግዝ ተስተውሏል። የኢሳት ባልደረባ የሆነ ጋዜጠኛ ወዳጄ ሁኔታውን ለመግለጵ የተጠቀመበት ቃል በህሊና ግርግዳዬ ላይ ተለጥፋ ቀርታለች። ጋዜጠኛው ” የየጁ ደብተራ ፣ ቅኔው ቢጐድልበት ቀራርቶ ሞላበት” ነበር ያለው።የህውሀት ልደትን ለመዘከር ወደ ደደቢት የተጓዘው እንግዳም ከብዙዎች ግምት በላይ ነበር። ታዳሚዎች የራሳቸውን አለም ፈጥረው በፈንጥዝያ ባሕር ውስጥ ሲዋኙ ነበር። የሀገሪቱን መንበረ ስልጣን ለብቻቸው የተቆጣጠሩት ህውሀቶች ” ሀገሬን አልረሳም!” በሚለው ተወዳጅ ዘፈን ሲጨፍሩ የተመለከቱ ደግሞ እስከ ዛሬም ከመገረም እንዳልወጡ አጫውተውኛል። በተለይም የጫካ ዘመኑን ” እንበር ተጋዳላይ!” በሚለው ቀስቃሽ ዘፈናቸው ያሳጠሩት ዘፋኞች ተቀምጠው ” ሀገሬን አልረሳም!” በሚል ኢትዬጲያዊ ዜማ መፈንጠዙ ከመጋረጃው በስተጀርባ ያለውን ለማወቅ አያዳግትም። እነ አቦይ ስብሀት ከዘመናት በኃላ ለመጀመሪያ ጊዜ ሸራተን ያገኙትን የዘፈኑ ባለቤት ” ስማ አንተ! …” ( ያልጨረስኩት ቃሉን ብጠራ በጣም አስቀያሚ፣ ኢትዬጲያ ብሆን ደግሞ ሶስት ወር ስለሚያሳስር ነው) …ለማንኛውም ሽማግሌው ስብሀት ” ስማ አንተ…”በማለት ያንቋሸሹትን ሰው እንዲዘፍን ሲያዙት የንቀት ደረጃቸውን የሚያሳይ ነው።

እንደዚህ አይነት መጠኑ ለግምት የሚያስቸግር ድግስ እና ሽብረቃ ያለበት የልደት አከባበር ያስቀናል። ያልሆኑትን ሆኖ በልጦ ለመታየት ፍላጐት ማሳደሩም አይቀርም። ያውም በ11% !!…ስለዚህ ብአዴን ይህን ማድረግ ነበረበት። የአማራ ህዝብ በግዴታ ገንዘብ ማዋጣት አለበት። መዋጮው የክልሉ ተወላጆች ብቻ ሳይሆኑ ሌሎችም መገደድ ነበረባቸው። ባጃጆች የበአሉ ማድመቂያ መሆን ነበረባቸው። የመንግስት ሰራተኛው የስራ ዋስትናውን በመያዣነት አስይዞ ሰላማዊ ሰልፍ መውጣት ነበረበት። ጡሩንባ እና ርችት የባህርዳርን ሰማይ ማድመቅ ነበረበት!

2• የህሊና እዳ!

ብአዴን ከግማሽ ቢሊዬን ብር የሚጠጋጋ ብር አውጥቶ ልደቱን በሚያከብር ሰአት ሀገራችን ያለችበት ሁኔታ አለምን ያስደነገጠ ሆኗል። ከ15 ሚሊዬን የሚሆኑ ዜጐቻችን የሚላስ የሚቀመስ ባጡበት ሰአት ይህን ያህል ገንዘብ አውጥቶ ልደት ማክበር ከታሪክ ለመማር ዝግጁ ካለመሆን የመጣ ነው። ንጉሱ ይህን አድርገዋል። ደርግም አድርጓል። ህውሀትም በብአዴን በኩል እያደረገው ነው። እዚህ ላይ እርግጠኛ መሆን የሚቻለው ችግሩ የተከሰተው ህውሀት እውነተኛ ልደቱን በሚያከብርበት የካቲት ወር ቢሆን ኖሮ አስረሽ ምችው ዙሩ አይከርም ነበር። ከንጉሱ እና ደርግ ጥፋቶች እርምት ወስደናል በማለት ውጫዊው ዳንኪራ ጋብ ይል ነበር።

የብአዴኑ ሊቀመንበር ደመቀ መኮንን ቤተሰቦች ቄያቸውን ነቅለው የተሰደዱበት የ67 ረሀብ በመቶ ሺዎች ህይወት ቀጥፏል። ድብቁ የወሎ ረሀብ በነበረበት ሰአት ንጉሰ ነገስቱ እጅግ ውድ የሆኑ እቃዎችን ስጦታ ያጋብሱ ነበር። የአዲሳአባ የመንገድ መብራቶች ልዩ ድምቀት እንዲሰጡ ተደርገው ነበር። በ77ቱ ረሀብ ደግሞ የኢሰፓ ምስረታ እና የአብዬቱ 10ኛው አመት በአል ከውጭ ሀገር በልዩ ትእዛዝ በመጣ ውስኪ እንዲደምቅ ተደርጓል። ዜጐች በተራቸው በተከሰተው ረሀብ እንደ ቅጠል ይረግፉ ነበር።

ዛሬ ደግሞ ቤተሰቦቹ በወሎ ረሀብ የተጠቁበት ጓድ! ደመቀ የትላንት ጠባሳውን ወደ ጐን ትቶ የሼሼ ገዳሜው የበላይ ጠባቂ ሆኗል። እያወቀ ከሚፈጵመው አስነዋሪ ድርጊት የመፀፀት እና የመታረም አዝማማሚያ አይታይበትም። ይባስ ብሎ ” ድርቁን ለህዝብ ንቅናቄ እንጠቀምበታለን” የሚል ክብረነክ ንግግር በአደባባይ ያሰማል። ሸክሙ የከበደው ህዝብ እንደሱ ዘመዶች ቄዬውን እየለቀቀ መሄዱን እየተመለከተ ችጋር የለም ይለናል። ፈረንጆቹ ለአለም ቀርፀው የሚያሳዩት የውርደት ሞት እየተመለከተ ” ሞት የለም!” ብሎ በጡንቻው እያሰበ መሆኑን ይነግረናል። …ኧረ ለመሆኑ ወዴት እየሔድን ይሆን?… የአድርባዬች እና ደናቁርት ስብስብ እስከ መቼ ፊታችን ይደነቀራል?… ወደ እንጦሮጦስ እየወረደች ያለችው ሀገራችንን የምንታደገው መቼ ይሆን?

ለማንኛውም የዛሬውን አጭር ማስታወሻ በአንድ አርፍተነገር መቋጨት ፈለኩ። ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ብአዴንን ሳስብ ፊትለፊቴ የመከደቀንብኝ አባባል ነው። አባባሉ የህውሀት ታጋይ የነበረው ገብሩ አስራት ነው። ገብሩ ” ዲሞክራሲ እና ሉአላዊነት በኢትዬጲያ” በሚለው መጵሀፏ ገጵ 135 ላይ ብአዴንን በተመለከተ የሚከተለውን ይለናል፣
” ኢህዴን/ ብአዴን ደርግን ለመጣል ካደረገው ወታደራዊ አስተዋጵኦ ይልቅ የፓለቲካ አስተዋጵኦው ይልቃል።”

Happy
Happy
0 %
Sad
Sad
0 %
Excited
Excited
0 %
Sleepy
Sleepy
0 %
Angry
Angry
0 %
Surprise
Surprise
0 %
    Print       Email
  • Published: 8 years ago on November 21, 2015
  • By:
  • Last Modified: November 21, 2015 @ 3:35 pm
  • Filed Under: Ethiopia

Average Rating

5 Star
0%
4 Star
0%
3 Star
0%
2 Star
0%
1 Star
0%
<"Without the support of our readers, the Maleda Times website would not exist in its present form">

You might also like...

በሰሜን ሸዋ ዞን ኤፍራታ እና ግድም ወረዳ መከላከያ ከአማራው ማህበረሰብ እና ከፋኖ ጋር ጦርነት ገጥሟል

Read More →

This site is protected by wp-copyrightpro.com

%d bloggers like this:
Skip to toolbar