www.maledatimes.com ደራሲና ጋዜጠኛ ነጋሽ ገ/ማርያም በ93 ዓመታቸው አረፉ - MALEDA TIMES
Loading...
You are here:  Home  >  Ethiopia  >  Current Article

ደራሲና ጋዜጠኛ ነጋሽ ገ/ማርያም በ93 ዓመታቸው አረፉ

By   /   July 21, 2017  /   Comments Off on ደራሲና ጋዜጠኛ ነጋሽ ገ/ማርያም በ93 ዓመታቸው አረፉ

    Print       Email
0 0
Read Time:2 Minute, 18 Second

ሰበር ዜና /  Shocking News by Getu Temesegen

ደራሲና ጋዜጠኛ ነጋሽ ገ/ማርያም በ93 ዓመታቸው አረፉ

 

#ETHIOPIA | Veteran journalist and author Negash Gebre-Mariam has died, aged 93.

 

(1917 – 2009)

 

• ሥርዓተ ቀብራቸው ነገ፣ ሐምሌ 11  ቀን 2009ዓ.ም በጉርድ ሾላ ሳህሊተ ምህረት ቤተክርስቲያን በ 9፡00 ሰዓት ይፈጸማል

 

***

 

በኢትዮጵያ ዘመናዊ ጋዜጠኝነት ታሪክ ከፋና ወጊዎቹ አንዱ ነበሩ፡፡ ከባህላዊው የጋዜጣ አዘገጃጀትና የገጽ ቅንብር እንደ ሥነ ጋዜጠኝነት ደርዝ ባለው አገባብ እነ አዲስ ዘመን ጋዜጣ መልክ እንዲይዙ በማድረግ ከሚጠቀሱት አንዱ ነበሩ፡፡

 

አቶ ነጋሽ ገብረ ማርያም ጋዜጠኛ ብቻም አልነበሩም፤ ባሕር ማዶ ተሻግረው እስከ ሁለተኛ ዲግሪ ድረስ የቀሰሙትን ለጋዜጠኞች የሥራ ላይ ትምህርት በመስጠትም አትርፈውበታል፡፡

 

ከግማሽ ምዕት ዓመት በፊት በአሜሪካ ሞንታና ዩኒቨርሲቲ የድኅረ ምረቃ ትምህርታቸውን አጠናቀው ከተመለሱ በኋላ በኢትዮጵያን ሔራልድና በአዲስ ዘመን ጋዜጦች በአዘጋጅነት በተከታታይ መሥራታቸው፣ በተለይ አዲስ ዘመን ጋዜጣ ከሳቸው መምጣት በፊት ለሁለት አሠርታት የቆየውን ልማዳዊ ቅርፅና አፃፃፍ እንዲለወጥ ማድረጋቸው ገጸ ታሪካቸው ያስረዳል፡፡

 

የጋዜጣውን ገጽ ቅንብር (ሌይአውት) የዜናና መጣጥፍ አቀማመጥ፣ ርዕሶች ሁሉ ሳይቀሩ ከዘመናዊው አሠራር ጋር እንዳስተዋወቁ ይነገራቸዋል፡፡

 

የጋዜጣው አቋም የሚንፀባረቅበትና ‹‹ኤዲቶሪያል›› ተብሎ ለዘመናት የቆየው ቃል ‹‹አማርኛ የለውም እንዴ?›› በማለት ጠይቀው በወቅቱ የጋዜጣው ባልደረባና በቤተክሀነት ትምህርት ሊቅ የነበሩት አፈ ሊቅ አክሊሉ ገብረ ኪሮስ ‹‹ርእሰ አንቀጽ›› የሚለውን ስያሜ እንዲያመጡ በማደረጋቸው ይወሳሉ፡፡

 

አቶ ነጋሽ አዲስ ዘመን ጋዜጣን ከለቀቁ በኋላ በኢትዮጵያ ሬዲዮና ቴሌቪዥን መምሪያ ረዳት ሥራ አስኪያጅ፣ በመቀጠልም የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ዋና ሥራ አስኪያጅ ሆነው አገልግለዋል፡፡

 

ከጋዜጠኝነት ሙያው በተጓዳኝም እንደ ወንድማቸው አሰፋ ገብረ ማርያም (እንደወጣች ቀረች ደራሲ) ደራሲ የነበሩት አቶ ነጋሽ፣ በፋሺስት ጣሊያን ወረራ (1928-1933) ላይ ጭብጡን ያደረገ ‹‹የድል አጥቢያ አርበኞች›› የተሰኘ ተውኔትም አቅርበዋል፡፡ ዕውቅናና ዝና ያተረፉበት ሁለተኛ የተውኔት ሥራቸው ‹‹የአዛውንቶች ክበብ›› በኢትዮጵያ ብሔራዊ ቴአትር መድረክ፣ እንዲሁም በኢትዮጵያ ቴሌቪዥን ቀርቧል፡፡

 

በሌላ በኩልም ስለሴተኛ አዳሪነት ምክንያትና መፍትሔ የተንፀባረቀበት ‹‹ሴተኛ አዳሪ›› ልቦለድ እናኑ አጎናፍር በሚል የብዕር ስም አሳትመዋል፡፡

 

የኢትዮጵያ ደራስያን ማኅበር ለሚሌኒየሙ ባሳተመው አጀንዳ ላይ እንደተመለከተው አቶ ነጋሽ ገብረ ማርያም፣ በ1917 ዓ.ም. በቀድሞው አጠራር በሐረርጌ ጠቅላይ ግዛት፣ በጨርጨር አውራጃ በሀብሮ ወረዳ፣ ልዩ ስሙ መቻራ በምትባል አካባቢ ነው የተወለዱት፡፡

 

በቄስ ትምህርተ ቤት የጀመሩት ትምህርት አስበ ተፈሪ ከተማ በመሄድ የአንደኛ ደረጃ ትምህርትን ቀጥለውበታል፡፡ ወደ አዲስ አበባ በመሻገርም በተፈሪ መኰንን ትምህርት ቤትና በመምህራን ማሠልጠኛ ተከታትለዋል በኮተቤ ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ትምህርታቸውን ካጠናቀቁ በኋላ በአሜሪካ ኢንፎርሜሽን ሰርቪስ ተቀጣሪ ሆነው ሠርተዋል፡፡

 

የሥራው አጋጣሚም በአሜሪካ ሞንታና ዩኒቨርሲቲ ለአራት ዓመት ጋዜጠኝነት እንዲማሩ አስችሏቸዋል፡፡ ከመንግሥታዊ መሥሪያ ቤቶች ጡረታ ከወጡ በኋላ በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ በትርፍ ጊዜ መምህርነት የጋዜጠኝነት ኮርስን ሰጥተዋል፡፡

 

ከመንግሥት ለውጥ በኋላ የፕሬስ ነፃነት መታወጁን ተከትሎ በመጣ የግሉ ሚዲያ ዘርፍ የአቶ ነጋሽ አስተዋጽኦ የሚጠቀሰው፣ የአዕምሮ ጋዜጣ አሳታሚ የነበረው ማህደር ኃላፊነቱ የተወሰነ የግል ማኅበር ባቋቋመው የጋዜጠኝነት ትምህርት ቤት ዋነኛ አስተማሪ ነበሩ፡፡

 

ባለትዳርና የሁለት ልጆች አባት የነበሩት አቶ ነጋሽ ባደረባቸው ሕመም ምክንያት ከዚህ ዓለም በሞት የተለዩት ሐምሌ 10 ቀን 2009 ዓ.ም. ሲሆን፣ ሥርዓተ ቀብራቸውም በሰአሊተ ምሕረት ቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን ይፈጸማል፡፡

 

***

እባክዎን፣ ይህንን ዜና እረፍት ሼር በማድረግ ለአገርና ለሕዝብ አድርሱልን፡፡

Happy
Happy
0 %
Sad
Sad
0 %
Excited
Excited
0 %
Sleepy
Sleepy
0 %
Angry
Angry
0 %
Surprise
Surprise
0 %
    Print       Email
  • Published: 7 years ago on July 21, 2017
  • By:
  • Last Modified: July 21, 2017 @ 11:05 am
  • Filed Under: Ethiopia

Average Rating

5 Star
0%
4 Star
0%
3 Star
0%
2 Star
0%
1 Star
0%
<"Without the support of our readers, the Maleda Times website would not exist in its present form">

You might also like...

በሰሜን ሸዋ ዞን ኤፍራታ እና ግድም ወረዳ መከላከያ ከአማራው ማህበረሰብ እና ከፋኖ ጋር ጦርነት ገጥሟል

Read More →

This site is protected by wp-copyrightpro.com

%d bloggers like this:
Skip to toolbar