www.maledatimes.com በእስረኞች ላይ ሽንት በመሽናትና ጥፍር በመንቀል የተጠረጠረችው መርማሪ 11 ክሶች ተመሠረቱባት - MALEDA TIMES
Loading...
You are here:  Home  >  Ethiopia  >  Current Article

በእስረኞች ላይ ሽንት በመሽናትና ጥፍር በመንቀል የተጠረጠረችው መርማሪ 11 ክሶች ተመሠረቱባት

By   /   February 10, 2019  /   Comments Off on በእስረኞች ላይ ሽንት በመሽናትና ጥፍር በመንቀል የተጠረጠረችው መርማሪ 11 ክሶች ተመሠረቱባት

    Print       Email
0 0
Read Time:1 Minute, 42 Second

በሽብር ወንጀል ተፈርጀው ታስረው በነበሩ የኦነግና አርበኞች ግንቦት ሰባት አባላት ላይ ሽንት በመሽናት፣ ጥፍር በመንቀልና በሌሎችም ዘግናኝ የተባሉ የወንጀል ድርጊቶች ተጠርጥራ የታሰረችው፣ የፌዴራል ፖሊስ ወንጀል ምርመራ የቀድሞ አባል ዋና ሳጅን እቴነሽ አረፉዓይኔ 11 ክሶች ተመሠረቱባት፡፡

ተከሳሿ በተለምዶ ማዕከላዊ ይባል የነበረውና በቅርቡ በተዘጋው የፌዴራል ፖሊስ ወንጀል ምርመራ ቢሮ የምርመራ ቡድን መሪና መርማሪ ሆና ስትሠራ፣ ካልተያዙ ግብረ አበሮቿ ጋር በመሆን በሽብር ተግባር ወንጀል ተፈርጀው በታሰሩ ዜጎች ላይ ፈጽማለች የተባለችውን የወንጀል ድርጊት፣ የፌዴራል ዓቃቤ ሕግ ለፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ያቀረበው ክስ ያስረዳል፡፡

ተከሳሿ ተመስገን ፀጋዬ፣ ወርቁ ፈረደ፣ ዘመነ ምሕረት፣ ሀብታሙ ሚልኬሳ፣ ዳንኤል እንየው፣ ጌትነት አማረ፣ አንሙት ታምሩ፣ ሽመልሽ አድማሴና ሌሎች ተጠርጥረው የታሰሩ ግለሰቦች ላይ የመመርመር ሥልጣን ሳይኖራት፣ ሌሊት በመጥራት ማሰቃየቷን፣ በሐሰት የእምነት ቃል እንዲሰጡና ሳያነቡ እንዲፈርሙ፣ ያልተያዘ ኤግዚቢት ላይ እንዲፈርሙ ስታስገድድና ስታስፈርም እንደነበር ክሱ ይገልጻል፡፡

ተጠርጣሪዎቹ ምንም ዓይነት ድርጊት እንዳልፈጸሙ ምላሽ ሲሰጧት፣ በማስመሪያ ፊታቸውን እንደመታቻቸው፣ በአፍንጫቸው እስክርቢቶ በማስገባትና ለረዥም ጊዜ እጃቸውን አሥራ በማንጠልጠልና ራቁታቸውን በጠባብ ክፍል ውስጥ ታስቀምጣቸው እንደነበር በክሱ ተገልጿል፡፡ ፂማቸውንና የብብታቸውን ፀጉር ፒንሳ በሚመስል ነገር  በመንቀል ራሳቸውን ስተው ሲወድቁ ውኃ በመድፋትና ‹‹ገና አፍህ ላይ እሸናብሃለሁ›› በማለት፣ ጀርባቸው ላይ ሽንቷን መሽናቷንና ከፍተኛ የሆነ የሰብዓዊ መብት ጥሰት መፈጸሟን ክሱ ያብራራል፡፡

‹‹የግንቦት ሰባት አርበኞች አባል ነን›› ብለው እንዲያምኑ ሱሪያቸውን በማስወለቅና የውስጥ ሱሪያቸውን በአፋቸው ውስጥ በመጠቅጠቅ፣ ብልታቸውን በማስመሪያ ትመታቸው እንደነበርም አክሏል፡፡ ተጠርጣሪዎቹን ከባድ ስፖርት በማሠራትና በመደብደብ፣ እንዲሁም ሁለት እጆቻቸውን በካቴና በማሰርና በግንብ ላይ በተሰካ ብረት ላይ በማንጠልጠልና በኤሌክትሪክ ገመድ በመግረፍ ቃላቸውን እንደተቀበለቻቸውም ክሱ ያስረዳል፡፡

ታሳሪዎቹን በጠረጴዛ ላይ በማስተኛት፣ በጥፊ በመምታት፣ ጀርባቸው ላይ ሽንቷን በመሽናት፣ የቪዲዮ ማስረጃ፣ መጻሕፍትና የኦነግ ዓርማ ከእነሱ እጅ የተገኘ መሆኑን አምነው እንዲፈርሙ ታስገድዳቸው እንደነበር ዓቃቤ ሕግ በክሱ ገልጿል፡፡ በስቴፕለር መምቻ ጭንቅላታቸውን በመምታትና ጎናቸውንም በመርገጥ ታሰቃያቸው እንደነበርም አክሏል፡፡

መርማሪዎቹ በጋራ በመሆን የታሳሪዎቹን እጆች በማሰርና በእጃቸው መሀል እንጨት በመክተት ገልብጠው በማቆየት፣ ውስጥ እግራቸውን በኤሌክትሪክ ገመድ እንደገረፏቸውና እንዳሰሯቸው ዓቃቤ ሕግ በክሱ ጠቁሟል፡፡ ተከሳሿ ተጠርጣሪዎቹን በኤሌክትሪክ ገመድ ከመግረፏም በተጨማሪ፣ በብረት ጉጠት የአውራ ጣታቸውን ጥፍር መንቀሏንም ዓቃቤ ሕግ በክሱ ጠቁሟል፡፡

በጠረጴዛ መካከል በማስገባት መዘቅዘቅ፣ ሽንቷን በሰውነታቸው ላይ መድፋት፣ በብልታቸው ላይ ውኃ እንደምታንጠለጥል በመንገር ታስፈራራና የሰብዓዊ መብጥ ጥሰት ስትፈጽም እንደነበር ዓቃቤ ሕግ በክሱ አብራርቷል፡፡ በአጠቃላይ ተካሳሿ ሥልጣኗን ያላግባብ በመገልገል በዋና ወንጀል አድራጊነት በፈጸመችው የማይገባ አሠራር መጠቀም ወንጀል መከሰሷን ዓቃቤ ሕግ በክሱ አብራርቷል፡፡    FacebookTwitterLinkedInShare

Happy
Happy
0 %
Sad
Sad
0 %
Excited
Excited
0 %
Sleepy
Sleepy
0 %
Angry
Angry
0 %
Surprise
Surprise
0 %
    Print       Email
  • Published: 5 years ago on February 10, 2019
  • By:
  • Last Modified: February 10, 2019 @ 12:15 pm
  • Filed Under: Ethiopia

Average Rating

5 Star
0%
4 Star
0%
3 Star
0%
2 Star
0%
1 Star
0%
<"Without the support of our readers, the Maleda Times website would not exist in its present form">

You might also like...

በሰሜን ሸዋ ዞን ኤፍራታ እና ግድም ወረዳ መከላከያ ከአማራው ማህበረሰብ እና ከፋኖ ጋር ጦርነት ገጥሟል

Read More →

This site is protected by wp-copyrightpro.com

%d bloggers like this:
Skip to toolbar