www.maledatimes.com …የጨርቆስ ወጣቶች እግዚአብሄር ከቁም ነገር ያብቃቸው። - MALEDA TIMES
Loading...
You are here:  Home  >  Ethiopia  >  Current Article

…የጨርቆስ ወጣቶች እግዚአብሄር ከቁም ነገር ያብቃቸው።

By   /   April 28, 2015  /   Comments Off on …የጨርቆስ ወጣቶች እግዚአብሄር ከቁም ነገር ያብቃቸው።

    Print       Email
0 0
Read Time:3 Minute, 3 Second

 

(ከፊልም ባለሙያው ያሬድ ሹመቴ ማስታወሻ) 

በትላንቱ ምሽት የሀዘን ቤት ቆይታዬ የሟቾቹ ቤተሰቦች ሲያጽናናቸው የሰነበተውን መላ ህዝብ እጅጉን ስሜት በሚነካ ሁኔታ አመስግነው አሰናብተዋል።

ከሰማዕታቱ መሀል የአንዱ እናት (የብሩክ) የሆኑትም እንዲህ አሉ ” እኔ (ሀገሬ) ኢትዮጵያን በጣም አመሰግናታለው። ልጄ እንደሞተም አልቆጥረውም።….. በህይወት እንዳለ ነው የምቆጥረው። በጣም ደስ ብሎኛል። በናንተ ፊት መቆም የሚገባኝም አይደለሁም። (በልጄ ምክንያት) እዚህ በመቆሜም እግዚአብሄርን አመሰግነዋለው። በጣም ደስ ብሎኛል። ብድር ይግባቹ እግዚአብሄር ይስጣቹ።”

“…የጨርቆስ ወጣቶች… መግለጽም ያቅተኛል። በጣም ነው ያስደሰቱኝ። እግዚአብሄር ከቁም ነገር ያብቃቸው። ልጄ አልሞተም በህይወት ነው ያለው።” በማለት በጉባኤው ላይ ለተሰበሰበው ህዝብ ከሌሎቹ የሰማዕታቱ ቤተሰቦች ጋር በጋራ በመሆን መጽናናታቸውን በመግለጽ ከዛሬ ጀምሮ ህዝቡ ወደዕለት ኑሮው እንዲመለስ አሰናብተዋል።

በምሽቱ ተጋባዥ አስተማሪ የነበሩትን የመምህር መጋቤ አዲስ እሸቱን ከመንፈሳዊነቱ ተጨማሪ ዘና የሚያደርገውን ትምህርት በጥቂቱ ላካፍላቹ።

“ሰው ብቻ አትሁኑ …..ሰው ብቻ ማለት ምንድን ማለት ነው? ብዬ ሳስብ፤ የሚበላ፣ የሚጠጣ፣ በሚለብሰው ልብስ፣ በሚነዳው መኪና የኑሮን ስኬት የሚለካ ማለት ነው። እስከ ሞት የሚኖር ማለት ነው፦ እንደ እንስሳ።

“…ታላቁ ሊቅ ዮሀንስ አፈወርቅ እንዲህ ይላል ‘ሰው እግዚአብሄር ሲለየው’ ይላል። ሰው ፈጣሪ ከሌላው ሲለየው፤ ጠባዩ እንደ አራዊት፤ አመጋገቡ እንደ እንስሳ፣ ሆኖ መልኩ ብቻ የእግዚአብሄር ሆኖ ይቀራል። በጣም ቀለል ባለ አገላለጽ ሲም ካርዱ የወጣ ሞባይል ማለት ነው። ጥሪ የማይቀበል። ለጉትቻ ማንጠልጠያ ብቻ የተሰራም ጆሮ አለ።”

“…እኔ በዕውነቱ ከተማው ፈርሶ እየተሰራ ነው እየተባለ አይናማዎቹ ሲያወሩም ሲያስወሩም እሰማለው። ፈርሶ መሰራት ያለበት የሰዉ አስተሳሰብ ነው።… የሰዉ አስተሳሰብ ፈርሶ ካልተሰራ፤ የተሰራ ከተማ ይፈርሳል። ጃፓንና ቻይና አገራቸውን ያለሙት መጀመሪያ አስተሳሰባቸውን አልምተው ነው። አስተሳሰቡ ያልለማ ህዝብ የለማውን ያወድማል።”

“…ምንድነው አሁን ያሳየሁዋቹ? (ትንሽ ጣታቸውን አውጥተው ወደላይ እያሳዮ) ይህች ጣት ብትታምም ሀኪም ቤት ብቻዋን ነው የምትሄው?… የማይመለከታቸው እነ ጉበት፣ እናፍንጫ፣ እነ እግር፣ አብረው ነው የሚሄዱት።”

“…ከረባት የሚታሰረው የት ላይ ነው?… አንገት ላይ የታሰረ ከረባት አካሄድን ይቀይራል። አሁን እግር ምን አገባው እውነት ለመናገር? (ከፍተኛ ሳቅ) ውድ መነጽር አይናቸው ላይ ያደረጉ ሰዋች አካሄዳቸውን ሁሉ ነው የሚቀየረው። አይን መነጽር ያደረገው መላ የሰውነት አካላትን ተክቶ ነው። ሰው እጁ ተቆርጦ ይኖራል፤ አይኑ ጠፍቶ ትኖራል። እራሱ ተቆርጦ ግን አይኖርም። 

“ቤታችሁ ገብታችሁ እንድታጤኑት ነው። እነዛ… (ምንትስ) የምንላቸው ክርስቲያኖችን አርደዋል ይባላል … ምዕራባውያኑ ደግሞ ክርስትናን እራሱን አርደውታል።….ወንድ ለወንድ፣ ሴት ለሴት፣ በቤተክርስቲያናቸው እያጋቡ፤ ክርስትናን አጋድመው ያረዱ ምዕራባውያን ናቸው። (ይህን ሁሉ ያመጣውም) የምዕራባውያን ልክ ያጣ ነጻነትና ገደብ ያለፈ ዝርክርክነት ነው።”

“…አንድ አንድ ጊዜ እመኛለሁ። እማይረባ እማይረባ ነገር ስናይ (ዓይናችንን) የሚያጠፋ ቆጣሪ ቢኖር… መልካም ነገር እስክናይ ድረስ ለጊዜው የሚያጠፋ ቆጣሪ ቢኖር እላለሁ…።

“አሁን እንደው ጆሮ በካርድ የሚሰራ ቢሆን ሀሜት እንሰማ ነበር?(ከፍተኛ ሳቅ)… የምንፈልገውን (ብቻ) አውርተን ስዊች ኦፍ እናደርገው ነበር። ስንት ዞማ ጸጉር ይዞ አስተሳሰቡ የከረደደ አለ።

“ጀርመን ሀገር ሄጄ ሲነግሩኝ፤ ባለ አምስት ኮከብ የውሻ ሆቴል አለ ተባለ። እኛ ሀገር አምስት ኮከብ ሆቴል ገብተው የበሉ ትንሽ ዝና (ሀብት) እና ትንሽ ስልጣን ያላቸው ናቸው። ማን ይገባል ከነሱ ውጪ። ግን ሰዋች ነን። የጀርመን ውሻ ዛሬም ውሻ ነው ለዘላለምም ውሻ ነው። እኛ ግን ሰው ነን። እንደ ሰው አስቡ (ምዕመናን) በማርያም።”

” እስኪ እንደው ትዳራችሁን ገምግሙት ደስተኛ ናችሁ? እንደሰው እየኖራችሁ ነው? ሚስቶቻችሁን ታከብራላችሁ? ፖለቲከኞቹ የኪነጥበብ ሰዎቹ (እዚህ) አላቹ ሲባል ሰምቻለሁ። ቆም ብላችሁ ልታስቡ ይገባል።”

” እኛም የሀይማኖት ሰዎች ሰበክን ሰበክን፤ ስብከቱ የህዝቡን አመለካከት መቀየር ትቶ የኛን ኑሮ ቀየረ።(ከፍተኛ ሳቅ)… የሰበክነው ሳይታወቅ እኛ እንታወቃለን። ማስታወቂያ ሰርተው ዝነኛ የሆኑ ሰዎች አሉ። ምርቱ ተሽጠ? ወይስ አልተሸጠም?” ማነው የሚያውቀው? (ከፍተኛ ሳቅ)

” ተርቦ ያበላን፣ በክራይ ቤት እየኖረ እኛን በቪላ ቤት ያኖረን፣ እሱ በግሩ እየሄደ ለኛ መኪና የገዛልንን፤ ዝነኛ ያደረገንን ህዝብ እኛ አመለካከቱን ልንቀይረው ይገባል። አለባበስን መቀየር ቀላል ነው አስተሳሰብን መቀየር ግን ዋጋ ያጠይቃል።”

“የግሪክ ፈላስፎች እነ ሶቅራጥስ የህዝቡን አመለካከር ለመቀየር ደከሙ። ዛሬ በኢኮኖሚ ውድቀት የምትንገላታ ግሪክ ናት፦ የነ ሶቅራጥስ ሀገር። ‘ሀገር ሲያረጅ ጃርት ያፈራል’ ይባላል። እኛ እንክዋን ይክበር ይመስገን ኢትዮጵያውያን ነን። …. “አሁንም ደግሜ እናገራለው። ይሄን ችግር ያደረሱብን ኢትዮጵያውያን አይደሉም። አብረውን የኖሩት ጎረቤቶቻችንን እነ መሀመድ እነ ከድጃ… ስጋዎቻችን፣ ደሞቻችን፣ አካሎቻችን ናቸው።”

“…ወቀሳ አበዛሁ?(የተሰበሰበው ህዝብ ከሳቅ ጋር አላበዙም አለ) ማርያምን?… ኮሶ የሚጠጣው ስለሚጣፍጥ አይደለም ስለሚያሽር(ስለሚያድን) ነው። ለመጣፈጥማ ስኩዋር ይሻል ነበር ግን ወስፋት ነው ትርፉ።” (ሳቅ)

አመሰግናለሁ።

የሀዘን ቤቱ ድባብ በደስታና በመጽናናት ተሞልቶ ሁሉም ወደ ህይወቱ ሊመለስ፤ መጽናናት የሚነበብባቸውን ቤተሰቦች ተሰናብተን ወጣን።
(ተዘገበ – ከጨርቆስ አዲስ አበባ)

Happy
Happy
0 %
Sad
Sad
0 %
Excited
Excited
0 %
Sleepy
Sleepy
0 %
Angry
Angry
0 %
Surprise
Surprise
0 %
    Print       Email
  • Published: 9 years ago on April 28, 2015
  • By:
  • Last Modified: April 28, 2015 @ 11:32 am
  • Filed Under: Ethiopia

Average Rating

5 Star
0%
4 Star
0%
3 Star
0%
2 Star
0%
1 Star
0%
<"Without the support of our readers, the Maleda Times website would not exist in its present form">

You might also like...

በሰሜን ሸዋ ዞን ኤፍራታ እና ግድም ወረዳ መከላከያ ከአማራው ማህበረሰብ እና ከፋኖ ጋር ጦርነት ገጥሟል

Read More →

This site is protected by wp-copyrightpro.com

%d bloggers like this:
Skip to toolbar