www.maledatimes.com “የሕወሓት የኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተክርስቲያንን ” የማፍረስ ዕቅድ (በዶ/ር አረጋዊ በርሄ) - MALEDA TIMES
Loading...
You are here:  Home  >  Ethiopia  >  Current Article

“የሕወሓት የኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተክርስቲያንን ” የማፍረስ ዕቅድ (በዶ/ር አረጋዊ በርሄ)

By   /   June 23, 2017  /   Comments Off on “የሕወሓት የኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተክርስቲያንን ” የማፍረስ ዕቅድ (በዶ/ር አረጋዊ በርሄ)

    Print       Email
0 0
Read Time:13 Minute, 6 Second

 

” ከፈረሱ አፍ ”
*★★★*

“የሕወሓት የኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተክርስቲያንን ” የማፍረስ ዕቅድ ( በዶ/ር አረጋዊ በርሄ )

ከመምህር ዘመድኩን በቀለ

” በጥንቃቄ ጊዜ ሰጥተን የምናነበው መረጃ ነው ” ። ይህ መረጃ ብዙ Share እና የብዙ ምሁራንን እና የእናት ቤተክርስቲያን ውለታ አለብን የሚሉ የቁርጥ ቀን ልጆቿን ጠንካራ አስተያየት ይፈልጋል ። የሠራነው ኮዲሚንየም ቢቀሙንስ ሀገር ቤት ስንገባ ከቦሌ ላይ ቢይዙንስ ብለው በኢህአዴግ እጅ መሞትን ፈርተው በስኳርና በደም ብዛት በልብ ድካምና በጉበት የሚሰቃዩ ሞትየማይቀርላቸው አስመሳይና ሆድ አደር አገልጋዮቿን እና በጭባጫ የስም ኦርቶዶክሳውያንን አይመለከትም ። እነዚህ ለውጡን ይፈልጉታል ነገርግን ለውጡ እንዲመጣ የሚፈልጉት ለሎች ሞተውና ታስረው እነሱ ከዚያ በኋላ የድል አጥቢያ አርበኞች በመሆን ነው ።

“በዚህ በዛሬው መረጃ ጥቃማቸው በሚነካባቸው ጥቂት አካላት ዘንድ ጫጫታ እና ስድብ ፣ ፍረጃና እርግምን እንደሚያስከትል የሚጠበቅ ቢሆንም ” ህልም ተፈርቶ ሳይተኛ አይታደርም በሚለው የአበው ብሂል መሰረት ስድብና ዛቻ ይመጣል ብዬ እውነት ከመናገር ወደ ኋላ ማለት ብሎ ነገር በእነ ዘንድ አይታሰብምና ይኸው ይልቅ ለመፍትሄው እንወያይበት ።

” ማስጠንቀቂያ የዛሬው ፖስቴ ለተቃዋሚዎቼም ፣ ለደጋፊዎቼም አስተያየት ለመስጠት መብቱን ሰጥቻቸዋለሁ ። ማንኛውም ሰው በዚህ ከ12 ሚልየን ህዝብ በላይ በሚመለከተው ፔጄ ላይ አስተያየት መስጠት ይችላል ። የምትሰድቡኝ ሰዎች ካላችሁም ” ደረጃዬን በሚመጥን መልኩ ሙልጬን ማውጣት በዚህ ፖስት ይፈቀዳል ። ያልገባችሁና ጉዳዩ የጠጠረባችሁ ሰዎች ባልገባችሁ ነገር ላይ ከመዘባረቅ ጮጋ ብትሉ ይመረጣል ።

” ይህን መረጃ በማቀበሌ ብቻ.! አንተ ፖለቲካ ውስጥ ለምን ትገባለህ.!?? አንተ ሃይማኖተኛ አይደለህም.! አንተን ብሎ ሰበኪ.! ምናምን ምናምን ጲሪረም ጳራራም ምንትስዮ ቅብጥርስዮ የምትል ኮማች እንደማልሰማህ ከወዲሁ እወቅ ። ይሄን የተበላበት ዕቁብ ለእትዬ ንገሯቸው ። አለቀ ። አራት ነጥብ ።

በፈለጋችሁት መጠን ማንንም መቃወም መብታችሁ ቢሆንም ህዝብን በጅምላ መስደብ በእኔ ፔጅ ላይ ክልክል ነው ። ከመስመር የወጣ ፀያፍ ስድብ እና ባልገባው ነገር ገብቶ የሚዘባርቅ ሰው ከተገኘ ” እንደተለመደው ” ከዚህ ጮማ የሆነ ትኩስ መረጃዎች ከሚገኝበት ፔጄ ላይ Block በተባለው የፌስቡክ ሰይፍ አማካኝነት ወገብ ዛላውን ጎምጄ ከፔጄ ላይ የማስወግደው መሆኔ ይታወቅ ዘንድ ለመግለፅ እወዳለሁ ። ዋ.! እንበጫበጫለሁ የምትል ሰገጤ ሁላ ምጥንቓቅ ማድረግ ይበጃችኋል ።



ቅድስት ኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ከፓትሪያርክ እስከ ጽዳት ሠራተኛ ” በአንድ ብሔርና በአንድ ቋንቋ ተናጋሪዎች ስር ለምን ወደቀች???

የቤተክርስቲያኒቱን የገንዘብና ሀብት በሙሉ የአንድ ቋንቋ ተናጋሪ ግለሰቦች ለምን እንዲቆጣጠሩት ተደረገ???

እንደ ሌሎቹ የመንግሥታዊም ሆነ የግል መሥሪያቤቶች ማለትም አየር መንገድ ፣ ቴሌ ፣ ባንክ እና በፌደራል መሥሪያቤቶች በመከላከያ ፣ በፖሊስ በፍርድ ቤቶች ያሉትን ወሳኝ ቦታዎችና ቁልፍ ቁልፉን ቦታዎች ሁሉ የትግርኛ ቋንቋ ተናጋሪዎች እንንዲይዙትና እንዲቆጣጠሩት እንደተደረገ ሁሉ በቤተክህነቱም አሁን ከዳቦ አልፈው ኬክ እየበሉ ፤ ከጠላ አልፈው ውስኪ እየተራጩ ፣ ከባዶ እግር ወደ V8 ከዳስ ወደ ቪላ እና አፓርታማ በሀብት ላይ ሀብት እንዲያከማቹ ፤ በግልፅም በአደባባይ እንዲዘርፉ ልዩ ፈቃድ ያላቸው እስኪመስል ድረስ መብት ተሰጥቷቸው ይታያሉ ።

ቅዱስ ፓትሪያርኩ ባለፈው ጊዜ ከሸገር ራዲዮ ጋዜጠኛዋ ከወሮ መዓዛ ብሩ ጋር ባደረጉት ቃለመጠይቅ በቤተ ክርስቲያኒቱ ውስጥ ስለተንሰራፋው ሙስና ሲጠየቁ ” አሱን መተው ይሻላል ፣ ጉዳዩ ከባድ ነው ። ከአንበሳ መንጋጋ ሥጋ እንደማውጣት ነው የሚቆጠረው ” በማለት መናገራቸውን ስናይ መጥፋት የሚችል ነገር ግን መንግሥቱ ይሄን ነገር ማጥፋት እንደሌለበት ቆርጦ መቀመጡን በግልፅ ያሳየናል ። እነዚህ ዘራፊዎች በዘራቸው ምክንያት ብቻ አይከሰሱም ፣ አይታሰሩም ፣ አይቀጡም ፣ የፈለጉትን ነገር የማድረግ ልዩ መብት አላቸው ።

እነዚህን ዘረኞች የሚቃወሙ የሰንበት ተማሪዎች ፣ ይታሰራሉ ፣ ይከሰሳሉ ፣ በፖሊስ ይደበደባሉ ፣ ሰንበት ትምህርት ቤቶቻቸው ይታሸጋሉ ። ካህናት ከሆኑም ከደረጃ ዝቅ ይደረጋሉ ፣ ይታገዳሉ ፣ ወይም ደግሞ በቅጣት መልክ ራቅ ወዳለ ሥፍራ እንዲመደቡ ይደረጋሉ ። ከዚህም ከፍ ካለ ብሄራቸውን ተገን በማድረግ የማሸማቀቅና እስከመታሰር የሚደርስ ግፍ ይፈጸምባቸዋል ።

አሁን የቤተክርስቲያኒቱ የሙዳየ ምጽዋት ገንዘብ በጥቂት ግለሰቦች እጅ እንዲገባ በመደረጉ ተጨማሪ ልማትና የካህናት ፣ የሰባክያነ ወንጌል የደሞዝ ጭማሪ የማይታሰብ ሆኗል ። በዚህም ምክንያት በግለሰቦች ቀጥተኛ ድጋፍ ካልሆነ በቀር ቤተክርስቲያኒቱ የስብከተ ወንጌሉን ለማስፋፋት የማትችልበት ደረጃ ላይ ደርሳለች ። አጠገባችሁ በሚገኝ አጥቢ ቤተክርስቲያን ውስጥ ከአለቃው ጀምሮ ዋና ጸሐፊው ፣ ቁጥጥሩ ፣ ቄሰ ገበዙ ፣ እናም በሊቃነ ጰጳሳት ደረጃም እንኳ ቢሆን አብዛኛውን ቁጥር የሚይዙት እነ ማን እንደሆኑ መገመቱ ነውር አይሆንም ።

በአሁን ወቅት እንዲህ ብሎ መናገር ጥቂት ጫጫታ ያስነሳል ተብሎ ቢገመትም ለነገዋ የቅድስት ቤተክርስቲያን ህልውና ሲባል ደፈር ብለን አይናችንን ጨፍነን እውነት እውነቱን ፤ ሀቅ ሀቁንም ካልተነጋገርን እና ለመፍትሄው ተግባራዊ እንቅስቃሴ ካልጀመርን ወዳጆቼ ነገን እንዳታስቡዋት ።

የቁልቢ ገብርኤልን ለ24 ዓመት እየመሩ ያሉት መነኩሴ ከክልሉ መንግሥት ጭምር ጥያቄ ቢነሳበቸውም እሳቸውን ከዚህ የወርቅ እንቁላል ከሚጥል ጋዳም ማንሳት ለህወሓት በህይወት እያለ የማይታሰብና የማይሞከር ነገር ነው ። የፓትሪያርክነት ፣ የአዲስ አበባ ሀገረስብከት ሃላፊነትና ገንዘብ የሚገኝባቸው አድባራትና ገዳማት በሙሉ በማን ቁጥጥር ስር እንዳሉ አናውቅም ማለት ግመል ሰርቆ አጎንብሶ እንደመሄድ ነው የሚቆጠረው ።

ለምሳሌ የአሲራ መቲራው መነኩሴና ብፁዕ አቡነ ዲዮስቆሮስ በጋራ ግንባር ፈጥረው እየሰሩ ያሉትን ቢዝነስ ስንመለከት ፤ እጅግ ውድ የሆኑ መኪናዎችን ከቀረጥ ነፃ በማስገባት የሚሠሩትን ቢዝነስ ስንመለከት ፤ ከተሃድሶ ፕሮቴስታንት አራማጁ የሮቶ ፋብሪካው ባለቤት ከአቶ ፀጋዬ ጋር የሚሰሩትን ቢዝነስ ስንመለከት፣ እጅግ ዘግናኝ ነገር ነው ። በተለይ ፈንዱን ከየት እንደሚያመጣው ባይታወቅም አቶ ፀጋዬ ሮቶ የአሰግድን እንቅስቃሴና በሃያት ኪዳነምህረት የመናፍቁ የአሰግድ ሳህሉ ደቀመዝሙር በሆነው” መኳንንት” በኩል ለካህናቱ እየተሰጠ ያለውን ስልጠና ስንመለከት ወደፊት የባሰ ነገር እንደሚገጥመን ልንረዳ ይገባል ።

ሌላ ምሳሌ እናንሳ.! ተወጋዡ ፓስተር አሰግድ ሳህሉ ቅዱስ ፓትሪያርኩን እና ሲኖዶሱን በአዲስ አበባ ጉባኤ ዘርግቶ ሙልጭ አድርጎ የሰደበበት ቪድዮ እጄ ገብቷል ። አሰግድ ይኽን ድፍረት ከየት ሊያመጣ ይችላል.?? ከኋላው አይዞህ ማን አባቱ ነው የሚነካህ የሚለው ከሌለ በቀር ምን አቅም ኑሮት ነው.?? ተመልከቱ በዓመት በሚልየን የሚቆጠር ዶላር የፈሰሰበትና 24 ሰዓት የሚሠራ የቴሌቭዥን ፕሮግራም ከሀምሌ 1 ቀን ጀምሮ በአየር ላይ ይውላል ተብሏል ። ይሄ ጉልበትና አቅም ከየት የተገኘ ይመስላችኋል????

እንግዲህ ቤተክርስቲያን ፈተናዋ በመላዋ ኢትዮጵያ መሆኑ መታወቅ አለበት ። በሽሬ ፣ በአድዋ ፣ በአዲግራትና በመቀሌ የሚታየው ፍጥጥ ያለው የመንግሥቱ አፍራሽ እንቅስቃሴ እንዲሁ ከመሬት ተነስቶ ድንገት የተፈጠረ አይደለም ። በደንብ ታስቦ እና ታቅዶ የተዘጋጁበት በጀትም ተይዞለት የተደረገ እንቅስቃሴነው ። በዓዲግራት ዩኒቨርሲቲ ” ነጠላ” መልበስ ፣ መስቀል ማጥለቅ ፣ ጥቅስ ያለበት ቲሸርት መልበስ የተከለከለውና የታወጀው የኦርቶዶክስን ሃይማኖት ከመሠረቱ ለማጥፋት ስለሚፈለግ ብቻ ነው ።

አብዛኛዎቻችን አሁን በጥንታዊቷ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ላይ እየተደረገ ያለው የማዳከምና የማፍረስ ሴራ እንደ እንግዳ ደራሽ ፣ እንደ ውኃም ፈሳሽ የሚመስለን ሰዎች ቁጥር ቀላል የምንባል አይነት አይደለም ። ይኽ ነገር ሆን ተብሎ ታስቦበትና በፖሊሲ ደረጃ ዕቅድ ወጥቶ ፕላን ተቀርጾለት በጀትም ተመድቦለት የሚሠራበት ሥራ እንደሆነም ተደጋግሞ ሲነገር እውነት የማይመስለን ሰዎች ጥቂት የምንባል አይደለንም ። ሆኖም ግን እውነታው እሱ ነው ።

ዛሬ የምንመለከተውም ይህንኑ ነው ። ይኽን ሴራ የሚነግረንም ከዚህ ሴራ ጠንሳሾች መካከል አንዱና ዋነኛው የነበረው ዶር አረጋዊ በርሄ ሲሆን ለድኩትርናው መመሪቂያ ባዘጋጀው ወረቀትና ኋላም በመጽሐፍ መልክ ተዘጋጅቶና ታትሞ ከወጣው መጽሐፍ ላይ ያገኘነውን መረጃ በማየት እርማችንን በማውጣት በቀጣይ ምን እናድርግ ፣ ምን ብናደርግስ ይህን ክፉ ሴራ በማክሸፍ የቤተክርስቲያንን የቀደመ ክብር ልንመልስ እንችላለን በሚለው ላይ ግልፅና ቀጥተኛ ውይይት ማድረግ መጀመር አለብን ። ” በሽታው ከታወቀ መድኃኒቱን ለማግኘት ጥቂት ቢያደክም እንጂ መፍትሄ አይጠፋለትም ።

ጥቂት ስለ ጸሐፊው ፦ እንደ መግቢያ…

በመጀመሪያዎቹ የህውሓት ምስረታ አካባቢ በድርጅቱ ውስጥ አውራጃዊነት (ሕንፍሽፍሽ) ተፈጥሯል በሚል ሰበብ “አሽዓ” (አክሱም ሽሬ ዓድዋ) ተብሎ የሚጠራና በእነ አቶ ስብሓት ነጋ የሚመራ ቡድን አብዛኞዎቹን ከሌላ የትግራይ አውራጃዎች ማለት ከእንደርታ፣ ከራያ አዘቦ፣ ከአጋሜና ከተምቤን አካባቢ የመጡትን ታጋይ ወጣቶች እስከመቷቸውና እስካስወገዷቸው ጊዜ ድረስ ዶክተር አረጋዊ በርሄ ከህወሓት መስራቾች አንዱና ከፍተኛ የሆነ አመራር የሚሰጥ የነበረም ሰው ነበር ።

በፈረንጆቹ የዘመን አቆጣጠር በ1985 ዓ/ም ከሌላኛው የህወሓት መስራች ከሆኑት ከአቶ ግደይ ዘርዓጽዮን ጋር ዶክተር አረጋዊ በርሄም ላይ ” ጋንግሪኖች ” የሚል ታፔላ ተለጥፎባቸው ከድርጅቱ እንዲወገዱ መደረጉም ይታወቃል ። በተለይም አቶ መለስ ሌሎች አስጊ ናቸው የሚላቸውን ሰዎች አፅድቶ ካጠናቀቀ በኋላ በሁለተኛው ምዕራፍ ላይ ጣቱን የቀሰረው በነ አቶ ግደይ ዘርአፅዮን ላይ ነበር። የድራማው ዋና ተዋናይም አቶ ስብሃት ነጋ እንደነበር የህወሓት ታሪክ በተመለከተ የተጻፉ የታሪክ ጸሓፍት በየመጻሕፍቶቻቸው የሳፈሩት ሀቅ ነበር ። በወቅቱ የክሱ ይዘትም “አረጋዊ በርሄ መለስን ለመግደል አሲሮ ነበር” የሚል በአቶ ስብሓት ነጋ የቀረበ የምስክርነት ቃል መነሻ ያደረገ እንደ ነበር ይታወሳል።

የሆነው ሆኖ በድርጅቱ ውስጥ ወንጀል የሠራ የውም መለስን ለመግደል አሲራችኋል ተብለው እስከ ሱዳን ድረስ ቀለብ ተሰፍሮላቸው የሄዱ ፤ ከመገደልም የተረፉትን እሊህ ሁለቱን ጎምቱ የህወሓት መስራቾችን ሳስብ ከዕድለኝነታቸውም ባሻገር የሆነ ደስ የማይልና ዛሬ የማልናገረው የሚሸት ነገር እንዳለ ሳልናገር አላልፍም ። ምክንያቱም ማርክስ ሌኒን ሊግ ትግራይ (ማሌሊት) በተመሰረተ ማግስት “የቻለ ይሩጥ ፣ ያልቻለ ያዝግም ፣ ያበቃለት ይለይለት” በሚል መሪ መፈክር ፀረ ኮሚኒዝም እየተባለ ታፔላ ተለጥፎበት የተባረረ ፣ የተመታ፣ የተሰወረና የታሰረ ታጋይ ቁጥሩ ቀላል እንዳልሆነ ይታወቃል ።

ከዚያው ከትግራይ ሳንወጣ የድርጅቱ ማእከላይ ኮሚቴ አባል የነበረው በአቶ ተኩሉ ሃዋዝ ላይ የተወሰደው የግዲያ እርምጃም ስንመለከት ፀረ ህወሓት/ማሌሊት አመለካከት ታራምዳለህ በሚል እንደነበር ብዙዎቹ ይስማማሉ ። ታዲያ ተቃራኒ ሃሳብ የሚያራምድን ግለሰብ ያውም የትግራይ ተወላጅ የሆነን ወንድማቸውን በሃሳብ ተሟግቶ ማሸነፍ ቢያቅታቸው በአደባባይ የገደሉ ሰዎች ፤ አቶ መለስን ለመግደል አሲረዋል ተብሎ ክስ የቀረበባቸው እና ” ጋንግሪን ” ስለሆኑ ይቆረጡ ፤ ተብለው የተፈረደባቸው አቶ ግደይ ዘርዓጽዮንና አቶ አረጋዊ በርሄን ስንቅ ቋጥሮ ፣ ቀለብ ሰፍሮ ፣ ጠባቂ ሰጥቶ በሱዳን በኩል አቋርጠው ወደ አውሮፓ እንዲሻገሩ መደረጉን ሳስብ ሰዎቹን ከዕድለኝነትም ባሻገር እንዲያው ዝም ብዬ ሌላ ነገር እንዳስብም ያደርገኛል ።

ለጊዜው ዛሬ የተነሳሁበት ዋና ዓላማ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያንን ለማዳከምና ለማፍረስ የሚደረገውን ክፉ ሴራ በተመለከተ ህወሓት ያራምድ የነበረውን ፖሊሲ ከጥንስሱ ጀምሮ ንቁ ተሳታፊ የነበረውነ አሁን የዶክትሬት ማእረግ የተጎናፀፈው አቶ አረጋዊ በርሄ ለዶክትርናው መመረቂያ ይሆነው ዘንድ ባዘጋጀውና በሚያስገርም መልኩ ምስክርነት የሰጠበትን ፤ ኋላም ላይ ይህ በራሱ በዶ/ሩ እጅ በመጽሐፍ መልክ የተዘጋጀው የመመረቂያ ጽሑፍ መጽሐፍ አንድ ወዳጄ እንዳነበው ይሰጡኛል ። ይኽ The political History of the Tigray people’s Liberation Front (1975 -1991) Revolt, Ideology and mobilization in Ethiopia የተሰኘ ርዕስ የተሰጠውና በ Aregawi Berhe PhD July 2009 የተጻፈ መጽሐፍ ብዙ ቁምነገሮችን እና እውነታዎችን የያዘ መጽሐፍ ቢሆንም እኔን ትኩረቴን የሳበው ግን ከገጽ 244 እስከ 246 የተዘረዘሩትና እናት ቤተ ክርስቲያኔን እምዬ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶን ለማዳከም በህወሓት ተረቅቆና ተዘጋጅቶ ተግባራዊ የተደረገው ሴራን የሚያጋልጠው ክፍል ነበር ትኩረቴን የሳበው ። እናም እኔም እኒሁ ወዳጄን እባክዎ ይህችን ክፍል በቻ ከፈረንጅ አፍ ወደ አማርኛ ይመልሱልኝ ፤ ይተርጉሙልኝም ብዬ በማስተርጎም የዶር አረጋዊን መጽሐፍ ታነብቡት ዘንድ በእንዲህ አይነት መልኩ ወደ አማርኛ አስተርጉሜ አቅርቤላችኋለሁና ተረጋግታችሁ በጥሞና ታነብቡት ዘንድ እለምናችኋለሁ ። ጎበዝ ማን ብቻውን ተቃጥሎ እና አርሮ ይቀራል.! እንግዲህ እናንተም አንብቡትና በጋራ እንቃጠላት እንጂ ። ይለይላችሁ እንግዲህ ።

ስእውነት በመጀመሪያው ወራቶች ላይ ፤ እዚህ አውሮፓ በስደት መቅረቴን ብዙም ባልወደውም ኋላ ላይ ግን የሚነበቡ መጻሕፍትን በገፍ የማገኝባቸው ወዳጆቼን መጠጋቴ እጅጉን እንደጠቀመኝ ሳልናገር ማለፍ አልፈልግም ። በተለይ ወደፊት እግዚአብሔር ካለ በዚሁ በእኔ ፔጅ በኩል እጅግ ግሩም የሆኑ መረጃዎችን በስፋት ማቅረቤ ሳስበው የተለየ ደስታ ጭምር እየተሰማኝ ስለመሆኑ ለመደበቅ አልሻም ። እድሜ ብቻ ይስጠን ። የኢትዮጵያ ሀገሬን እና የተዋሕዶ ሃይማኖቴን ትንሣኤያቸውን ሳያሳየኝማ አይግደለኝ። አደራውን ፈጣሬዬን እለምነዋለሁ ።

ለዛሬ ተርጓሚዬን ከልብ እያመሰገንኩኝ ይኽን ጦማር ስጋብዛችሁ እጅግ ከፍ ያለ ደስታ እንደሚሰማኝ ስገልጽ ራሱ እጅግ ደስ እያለኝ ነው ።

★★

Neutralizing the Church and mobilizing Muslims
Neutralize meaning: make (something) ineffective by applying an opposite force or effect.

(ኒውትራላይዝ ) የሚለዉን የእንግሊዝኛ ቃል መዝገበ ቃላቱ ሲፈታው ፤” አንድን ነገር ዉጤታማ እንዳይሆን ተፃራሪ ኃይል ወይም ኹነት ላዩ ላይ ማድረግ ወይም ማከል፤ በማለት ይተረጉመዋል” ። እናም በዚህኛው አገባብ ቤተክርስቲያንን እንዳልነበረች ማድረግ ብሎ መውሰድ እውነታውን ፍንትው አድርጎ ያሳያል)

The Church (ቤተ ክርስቲያኒቱ) የተደበላለቁ (የተለያዩ) ምክንያቶች በህውሓት እና በቤተ ክርስቲያኒቱ መካከል የነበረዉን ግንኙነት አስቸጋሪ አድርገዉታል። በቅድሚያ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተ ክስርቲያን ለዘመናት በመንደሩ ማኅበራዊ ሕይወት ዉስጥ ማዕከላዊ ሆና ኖራለች። ጋብቻዎች፤ ሥርዓተ ክርስትናዎች (ጥምቀት)፤ የቀብር ሥርዓት እንዲሁም በጎረቤታሞች መካከል እንኳ ግጭት ሲኖር ሁሉ ሽምግልናው የሚከናወነው በቤተ ክርስቲያኒቱ አማካኝነት ነው ። እናም በቁጥር በርከት ያሉ ቀሳዉስት በየአጥቢያው ይህን የቤተ ክርስቲያን አገልግሎት ለማከናወን ይገኙ ነበር። እያንዳንዱ ቤተሰብ ሃይማኖታዊ ሕይወቱን የሚንከባከብ የራሱ የሆነ የሃይማኖት አባት ( የንስሃ ወይም የነፍስ አባት ማለታቸው ነው) ካህን አለው ።እናም ይህ ካህን በእያንዳንዱን የተለየ የሕይወት ዑደት ዝግጅት ላይ ተገኝቶ ቡራኬውን እንዲሰጥ ይጠራል ( በጋብቻ፣ በልደት ፣ በሞት ፣ በኃዘን ፣ በደስታ) ብቻ በሁሉም የማኅበረሰቡ እንቅስቃሴ ውስጥም ቤተ ክርስቲያኒቱ በዚህ መልክ በእያንዳንዱ ቤተሰብ ጋር ተቆራኝታለች።

በሁለተኛ ደረጃ፤ ቤተ ክርስቲያኒቱ በሕዝቡ እና በመንግሥቱ መካከል ያለዉን ግንኙነት መሥርታለች። ካለፉት ነገሥታት ጎንም በየዘመናቱ ቆማለች። በየጊዜዉም የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን እድገት፣ ሕልውና በማፅናት ካስፋፉት ካለፉት የኢትዮጵያ ነገሥታት ጎንም ትቆም ነበር። ቤተ ክርስቲያኒቱ ከመንደር አንስታ እስከ ብሔራዊው ማዕከል ድረስ በተዋረድ የተደራጀች ነበረች ። እናም ይህ ለሃይማኖታዊና ማኅበራዊ እና ባህላዊ ሕይወት መሠረት ሆኗል። የቤተ ክርስቲያኒቱ ተቋም በኅብረተሰቡ ሕይወት ብቻ ሳይሆን በተቀናቃኝ ኃይሎች ፤ በመንግሥት እና አማፅያን መካከል እንኳን ሳይቀር ለሚፈጠር ጠብ እና ግጭት ሳይቀር በሽምግልና ወሳኝ የሆነ ሚና ስትጫወት ኖራለች።

ቤተ ክርስቲያኒቱ ተከታዮቿ የሆኑ ምዕመናን የኢትዮጵያን መንግሥት የሚመሩትን እንዲያከብሩ ታስተምራለች፤ በዚህም ምክንያት እንደ ሰንደቅ ዓላማ ያሉ ብሔራዊ ትዕምርቶች (ምልክቶች) በሃይማኖታዊም ሆነ ማኅበራዊ ዝግጅቶች ላይ መጠቀም በብሔራዊ ደረጃ ከስምምነት ላይ የተደረሰበት የጋራ መግባባት ነበራት። የትኛውም ቤተ ክርስቲያን የኢትዮጵያ ሰንደቅ ዓላማ የሌለበት ትልቅ ክብረ በዓል አክብሮ አያውቅም። ይህ ደግሞ በኢትዮጵያ ጦር ሠራዊትም የሚዘወተር መደበኛ ተግባር ነው ።

ሦስተኛ፤ የየትኛውንም የኢትዮጵያ ንጉሥ ሕጋዊነቱን የምታፀና ዋነኛዋ አካል ቤተ ክርስቲያኒቱ ነበረች ። ኢትዮጵያ ዉስጥ ነገሥታትን የመቀባቱ ሥርዓት ትግራይ አክሱም ውስጥ በምትገኘዉ በአክሱም ጽዮን ቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን የማከናወን ሥርዓትም ነበር ። ነገሥታቱም ቤተ ክርስቲያኒቱ ለምታደርገዉ ድጋፍም ፤ ለገዳማቱና ለአድባራቱ ርስተ ጉልት በመስጠት ወሮታ ይከፍላሉ ። በዚህም ምክንያት ገዳማትና አድባራቱ ከጉልት መሬቱ አንድ ሦስተኛዉን እጅ ይወስዳሉ። ተራው የአካባቢዉ ነዋሪ ሕዝብም ለቤተ ክርስቲያኗ መጠበቂያ ( መደጎሚያ) መሬት ይመድቡ ነበር። ካህናትም ለሚሰጡት አገልግሎት በዚህ አማካኝነት ይከፈሉ ነበር። መሬት ዋነኛው ማበረታቻ ስለነበርም በርካታ ወጣት ወንዶች ካህን ለመሆን አብዛኛዉን ጊዜያቸዉን ወደ ቤተ ክርስቲያን ትምህርት ቤት በመሄድ ያሳልፉ ነበር። በየአጥቢያው የሚያገለግሉት ካህናትም ለዚሁ አገልግሎታቸው መሬት ይሰጣቸውም ነበር።

የቤተ ክርስቲያኗ እና የመሬት አስተዳደር በገበዙ እጅ ውስጥ ነበር። ገበዝ የሚሆነው ሰው ካህን ወይም ተራ ሰው ሊሆን ይችላል። ሆኖም በማኅበረሰቡ ይመረጥና በቤተ ክርስቲያን ሓላፊነቱ ይጸድቅለታል። በ1966 ዓም ንጉሣዊው ሥርዓት ወድቆ ወታደራዊው ኃይል ሥልጣን ከያዘ በኋላ የመንግሥትና የቤተ ክርስቲያን ትስስር አከተመ። ደርጉ ሶሻሊዝምን አወጀ፤ የቤተ ክርስቲያኗን መሬትም ሁሉ ወረሰ። በወቅቱ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ፓትሪያርክ የነበሩት አቡነ ቴዎፍሎስም ታሰሩ፤ ቆየት ብሎም ሥልጣን ላይ በነበሩት ኃይሎች ተገደሉ። በ1967 ዓም ቤተ ክርስቲያኒቱ ማርክሲስት በነበረው ወታደራዊ አገዛዝ ፤ በግራ ክንፍ የትጥቅ ትግሎች እና በሰሜን በነበሩት እንቅስቃሴዎች ምክንያት አጣብቂኝ ውስጥ ገባች። በመጀመሪያ አካባቢ እንደ ኢዲዩ ባሉት የቀኝ ዘመም ንቅናቄዎች ቤተ ክርስቲያኗ ተስፋ ጥላ የነበር ቢሆንም ኋላ ላይ ግን ምንም የተገኘ ውጤት አልነበረም።

★★በተጨባጭ እንቅስቃሴ ላይ የሚያተኩረው ህወሓት ቤተ ክርስቲያኒቱ በመንደር ማኅበራዊ ሕይወት ውስጥ ያላትን ሚና እና ለሀገር አንድነት ያላትን ድጋፍ በሚገባ ተረድቷል። በዚያም ላይ ሶሻሊዝምን ፣ መሬት መወረሱን እንዲሁም መንግሥትን በሚቃወሙ ኃይሎች እና በቤተ ክርስቲያኗ መካከል ሊኖር የሚችለውን ኅብረትም ተገንዝቧል። ስለዚህም ቤተ ክርስቲያኒቱ በህውሓት መንገድ ላይ እንደቆመች ፤ ነገር ግን በጥንቃቄ መያዝ እንደሚኖርባት ታይታለች።

★★ህውሓት ምንም እንኳን ርዕዮተ ዓለሙ ማርክሲስት ቢሆንም ያን ያህል ፀረ ሃይማኖት ሆኖ አያዉቅም ። ያም ቢሆን ግን ለራሱ ዓላማ ሲል ቤተ ክስቲያኒቱን በሥሩ ታዛዥ ለማድረግ መፈለጉ ቅንጣት ያህል ጥርጥር የለዉም ። በዚህም ምክንያት ህውሓት ቤተ ክርስቲያኗ ያላትን ተጽዕኖ ለማፈራረስ የተቀናጁ ተከታታይ ርምጃዎችን ወስዷል።

የመጀመሪያዉ፤ እርምጃ ደርግ የወሰደዉን መሬትን የመዉረስ ርምጃ ማፅናት፤ይኸም የቤተ ክርስቲያኒቱን የኢኮኖሚ አቅም ያሳጣል፤ ሌላዉ እንደ ኢዲዩ ያሉ ሀገራዊ የቀኝ ክንፍ እንቅስቃሴዎች ደግሞ ያንሰራራሉ የሚለዉን ተስፋ ማጥፋት።

ለዘመናት የቆየዉ የቤተ ክርስቲያኒቱ ኢኮኖሚ በዚህ መልኩ ተሰበረ ። በዚህ ምክንያትም ቤተክርስቲያኒቱ ከተከታዮቿ ጋር አዲስ ማኅበራዊ ውል ለመግባት ተገደደች ። የጉልት መሬት አወዛጋቢነቱ ቀረ ፤ በዚህ ምክንያትም ገበሬዎች ካህናት ለሚሰጧቸዉ አገልግሎት መሬታቸውን በማረስ ይከፍሏቸው ጀመር። እንዲህ ያለዉ መሬት መወረሱ ከቤተ ክርስቲያን ብቻ ሳይሆን ከኅብረተሰቡም ተቃዉሞ አስነስቷል። መሬት በተከፋፈለበት በመጀመሪያዎቹ ጊዜያትም ለቤተ ክርስቲያን የተሰጡት መከፋፈላቸውን የመቃወም ሁኔታም ነበር። በኅብረት የተነሳዉ ተቃውሞ ያሰጋው ህውሓት መሬቶቹ በአካባቢዉ ይዞታ እንዲቆዩ በማድረግ የቤተ ክርስቲያኒቱን አስፈላጊነት እንደሚቀበል እንደማረጋገጫ ተጠቅሞበታል።

በሁለተኛ ደረጃ ማኅበራዊ እና ኢኮኖሚያዊ ትኩረት ከቤተ ክርስቲያን ይልቅ ወደ ሰዎች ስብስብ እንዲዞር የማድረግ ሙከራ ነበር። አስተዳደራዊ እና ማኅበራዊ እንቅስቃሴ ሁሉ በማኅበራት ተወሰደ፤ ሌላዉ ቀርቶ የቤተ ክርስቲያን ጉዳይ፣ መብትና ግዴታዋ፣ እንዲሁም ተከታዮቿ ሁሉ በማኅበራቱ ውሳኔ ስር ወደቁ።የቤተ ክርስቲያኒቱ ሕዝቡን የማንቀሳቀስና ተጽዕኖ የማሳደር አቅም ሁሉ እጅግ ቀነሰ። ቤተ ክርስቲያኗ ግጭቶችን የመሸምገል ደረጃ፣ መንፈሳዊነት እና በቤተሰብ ጉዳዮችም ሁሉ የነበራትን መብት አጣች። ምክንያቱም አዲሶቹ የፖለቲካ ባለስልጣናት ይህን አካሄዷን ፈጽሞ አይፈልጉትምና ነው።

ሦስተኛው ፦ ህወሓት በ1969 ዓም ተከታታይ አውደ ጥናቶች እና ስብሰባዎችን ለተመረጡ የአጥቢያ ካህናት አዘጋጀ። የአውደ ጥናቱ ዋና ዓላማ በህወሓት እቅድ መሠረት የትግራይን ብሔርተኝነት በመገንባት፤ የትግራይን ቤተ ክርስቲያን ከሰፊዉ የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ለመነጠል ነበር። የተጨቆነዉ የትግራይ ብሔርተኝነት ተፅዕኖ ፈጣሪዋን የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን የሚፈታተን ነበር።

★ ለካህናት የተዘጋጁት የመጀመሪያዎቹ የወረዳ ዐውደ ጥናቶች ከአዲስ አበባ የሥነመለኮት ኮሌጅ በተመረቀዉ በአንደበተ ርቱዑ “የህወሓት ተዋጊ” * ገ/ኪዳን ደስታ * ነበር የተሰጡት። የአዉደ ጥናቱ ርዕሰ ጉዳይም የኢትዮጵያን ቤተ ክርስቲያን አስተዳደር (ሥልጣን) በህወሓታዊ አስተሳሰብ በተቃኘች ቤተ ክርስቲያን መተካትና የቤተ ክርስቲያኒቱንም ቋንቋ ትግሪኛ ማድረግ ፤ በሂደትም ግቡ የትግራይ ብሔርተኝነትና ማንነት እንዲኖራት ማድረግ። ሂደቱም በአጥቢያ ካህናትንና ተራ ክርስቲያኖችን በብሔራዊ ደረጃ ካለችዉ የቤተ ክርስቲያን ተዋረድ መገንጠልንም ያካተተ ነበር።( እዚህ አካባቢ ተደጋግሞ ይነበብ ) ።

የቤተ ክርስቲያኒቱን ሥልጣን ለማዳከምምበስብሃት ነጋ የሚመራ የስለላ ቡድን ተቋቋመ። ይህ ቡድንም ትግራይ ውስጥ ባሉት ★ደብረ ዳሞን ጨምሮ የቆዩ ገዳማት ውስጥ መነኩሴ መስለው የህወሓት አባላት እንዲገቡና ህወሓት በሚፈልገዉ መንገድ ቤተ ክርስቲያን ላይ ጫና የሚያሳድሩ እንቅስቃሴዎችን እንዲያከናውኑ ተደረገ።

በ1979 እና በ1981ዓም በህወሓት ፕሮግራም የትግራይን ቤተ ክርስቲያን ለመቅረፅ በየወረዳዉና በብሔር ደረጃ ህወሓት ነፃ ባወጣቸዉ አካባቢዎች የካህናት ጉባኤ ተካሄደ። ነፃ በወጡት የትግራይ አካባቢዎች በህወሓት መመሪያ ሥር የሚሠራ ***የተለየ*** የኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ጽሕፈት ቤት ተቋቋመ። በተግባርም የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን በሁለት አስተዳደራዊ ጽሕፈት ቤቶች ተከፈለች።

አንደኛዉ በአገዛዙ ሥር ሌላኛዉ በህወሃት ሥር። ሁለቱም እስከ 1982 ድረስ ትግራይ ውስጥ ሲሠሩ ነበር። ህወሓት መቀሌን ሲቆጣጠር የአገዛዙ አስተዳደርም ጽሕፈት ቤትም ከመቀሌ ሸሽቶ ወደ ደሴ ሄደ። ነፃ በወጡት አካባቢዎች የነበረዉ አስተዳደራዊ ጽሕፈት ቤትም መቀሌ ገባ። ከዚያም ህወሓት በ1983 ዓም የሀገሪቱን ሥልጣን እስኪይዝ ድረስ ቆየ።

ዶር አረጋዊ በርሄን አስከ 1983 ዓመተ ምህረት ድረስ ያለውን የህውሓትን ተንኮልና ሴራ በመጠኑም ቢሆን የነገረንን ሁሉ በልቦናችን እንዲያሳድርብን እየጸለይን ፤ ከ1983 በኋላ እስከ አሁን ድረስ ያለውንና በለፉት 26 ዓመታት በሙሉ በቅድስት ቤተክርስቲያናችን በተዋሕዶ ሃይማኖታችን ላይ እየተፈጸመባት ያለውን ግፍ እንዲሁም ቅድስት ቤተ ክርስቲያን እያሳለፈች ያለውን እጅግ ፈታኝ መከራ ደግሞ መስካሪና ነጋሪ ሳያስፈልገን ይኸው እኛው በአይናችን እያየነው ያለው ሃቅ ስለሆነ ነጋሪ አያሻንም ።

” እኔ ግን እላለሁ !!! እምዬ ኦርቶዶክስ አንቺ እናትዓለም ፤ የእነ ቅዱስ ዲዮስቆሮስ ፣ የእነ ቅዱስ አትናቴዎስ እና ቅዱስ ቄርሎስ የእነ ቅዱስ ጊዮርጊስ ፣ የእነ ቅድስት አርሴማ ፣ የእነ አቡነ ተክለሃይማኖት ፣ የእነ አቡነ ገብረመንፈስ ቅዱስ ፣ የአባ ሳሙኤል ዘዋልድባና የአቡነ አረጋዊ ሃይማኖታቸው የሆንሽ ንጽህት ተዋሕዶ ሃይማኖቴ ሆይ ! ብረሳሽና ብከዳሽ ቀኜም ትርሳኝ፣ ትክዳኝም ። ባላስብሽና ባልሞትልሽ ምላሴ ከጉሮሮዬ ይጣበቅ ። ሳለጎበድድ ሳለከዳሽ እንድኖር አምላክሽ ይርዳኝ ። ይህን ባለደርግና ሳልጮህልሽ ዝም ብዬ ብሞት ስሜ ከህይወት መጽሐፍ ይደምሰስ ።

“ጌታ ሆይ! ከዚህ በፊት በሆነው ፤ አሁንም እየሆነ ባለው እና ወደፊትም በሚሆነው ነገር ፤ ክብሩን ሁሉ አንተ ውሰድ ።” አሜን. !

“ድንግል ሆይ እናቴ ! አዛኝቱ ዛሬም እንደትናንቱ ቅደሚ ከፊት ከኋላዬ ”

ይህንንም ራሴው በእጄ ጻፍኩት ። 004915217428134 ደግሞ የቫይበር ፣ የኢሞና የኋትስአፕ መልእክቶችን የምቀበልበት የእጅ ስልኬ ነው ።

ሻሎም.! ሰላም.!

ዘመድኩን በቀለ ነኝ ።
ሰኔ 16/2009 ዓም
ከራየን ወንዝ ማዶ.!

Happy
Happy
0 %
Sad
Sad
0 %
Excited
Excited
0 %
Sleepy
Sleepy
0 %
Angry
Angry
0 %
Surprise
Surprise
0 %
    Print       Email
  • Published: 7 years ago on June 23, 2017
  • By:
  • Last Modified: June 23, 2017 @ 1:02 pm
  • Filed Under: Ethiopia

Average Rating

5 Star
0%
4 Star
0%
3 Star
0%
2 Star
0%
1 Star
0%
<"Without the support of our readers, the Maleda Times website would not exist in its present form">

You might also like...

በሰሜን ሸዋ ዞን ኤፍራታ እና ግድም ወረዳ መከላከያ ከአማራው ማህበረሰብ እና ከፋኖ ጋር ጦርነት ገጥሟል

Read More →

This site is protected by wp-copyrightpro.com

%d bloggers like this:
Skip to toolbar