www.maledatimes.com ሰበር ዜና – ቅ/ሲኖዶስ ለጥር 6 አስቸኳይ የምልአተ ጉባኤ ስብሰባ ጠራ - MALEDA TIMES
Loading...
You are here:  Home  >  Ethiopia  >  Current Article

ሰበር ዜና – ቅ/ሲኖዶስ ለጥር 6 አስቸኳይ የምልአተ ጉባኤ ስብሰባ ጠራ

By   /   January 1, 2013  /   Comments Off on ሰበር ዜና – ቅ/ሲኖዶስ ለጥር 6 አስቸኳይ የምልአተ ጉባኤ ስብሰባ ጠራ

    Print       Email
0 0
Read Time:8 Minute, 57 Second
  • በሀገር ውስጥና በውጭ ያሉ ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት ለታሪካዊና ወሳኝ ጉባኤ ተጠርተዋል
  • አደራዳሪው አካል በአዲስ መልክ ተደራጅቶ የዕርቀ ሰላም ሂደቱ እንደሚቀጥል ይጠበቃል
  • የፓትርያሪክ ምርጫ ሕገ ደንቡ የጸደቀበት እና አስመራጭ ኮሚቴው የተቋቋመበት መንገድ ዳግመኛ ይታያል
  • በአ/አ የቀሩት የሰላም ልኡክ መ/ር አንዷለም ዳግማዊ ከዐቃቤ መንበሩ ጋራ ተወያዩ

ቋሚ ቅዱስ ሲኖዶስ ዛሬ፣ ታኅሣሥ 23 ቀን 2005 ዓ.ም ጠዋት ባካሄደው ስብሰባ የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ ለጥር 6 ቀን 2005 ዓ.ም እንዲጠራ ወስኗል፡፡

አስቸኳይ የምልአተ ጉባኤው ስብሰባ÷ የዕርቀ ሰላም ንግግሩ ቅድሚያ ትኩረት ተሰጥቶት በአዲስ አነጋጋሪ አካል ስለሚቀጥልበት ኹኔታ፤ ታኅሣሥ 8 ቀን የጸደቀው የፓትርያሪክ ምርጫ ሕገ ደንብ እና አወዛጋቢው የፓትርያሪክ አስመራጭ ኮሚቴ የተቋቋመበትን መንገድ ከቀኖና ቤተ ክርስቲያን፣ ከሕገ ቤተ ክርስቲያን እንዲሁም ከዕርቀ ሰላሙ ሂደት አኳያ ያለውን አግባብነት ዳግመኛ በማጤን ለቤተ ክርስቲያኒቱ ሰላምና አንድነት ወሳኝና ታሪካዊ የኾነ ውሳኔ እንደሚያሳልፍ ይጠበቃል፡፡

በዚሁ ወሳኝና ታሪካዊ ውሳኔ ይተላለፍበታል ተብሎ ለሚጠበቀው አስቸኳይ የምልአተ ጉባኤ ስብሰባ÷ በሀገር ውስጥና በውጭ አህጉረ ስብከት ለሚገኙ፣ በቅ/ሲኖዶሱ ስብሰባ ላይ መሳተፍ ለሚችሉ ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት ጥሪው እንደሚተላለፍላቸው ተገልጧል፡፡ በቅዱስ ሲኖዶሱ የስብሰባ ሥነ ሥርዐት መሠረት÷ ሃይማኖትንና ቀኖና ቤተ ክርስቲያንን በሚመለከት ጉዳይ ከጠቅላላው አባላት ከአራት ሦስት እጅ መገኘት ይገባቸዋል፤ አስተዳደርን የሚመለከት ሲኾን ደግሞ ከጠቅላላው አባላት ከሦስት ሁለት እጅ መገኘት ያስፈልጋቸዋል፡፡

አሁን ምልአተ ጉባኤው ለአስቸኳይ ስብሰባ የተቀጠረባቸው አጀንዳዎች (የዕርቀ ሰላሙ አጀንዳዎችና አቋሞች፣ የፓትርያሪክ ሹመትና የምርጫ ሕገ ደንቡ) በአንዳንዶች ዘንድ አስተዳደራዊ ይዘቱ አመዝኖ ቢነገርም በተለይም በሹመት ቀደምትነት ባላቸው በርካታ አረጋውያን ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት ዘንድ የቀኖና ቤተ ክርስቲያን ጉዳይ ኾኖ በመወሰዱ ቅ/ሲኖዶሱ በተሟላ ቁጥር ተገኝቶ በስምምነት እንዲወስንባቸው ማስፈለጉ ተዘግቧል፡፡

ቅዱስ ሲኖዶሱ ምልአተ ጉባኤ ኾነው በቋሚነት የሚሰበሰቡ 51 ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት (ከእኒህ ሦስቱ በሕመምና በዕርግና) ያሉት ሲኾን በታኅሣሡ ስብሰባ ‹‹ስንጠራችኹ ትመጣላችኹ›› በሚል እንዳይገኙ የተደረጉት በውጭ አህጉረ ስብከት የሚገኙ ከዐሥር ያላነሱ ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት ለጥር 6 ቀን የአስቸኳይ ምልአተ ጉባኤ ስብሰባ ላይ መጠራታቸው የግድ እንደኾነ ተነግሯል፡፡

ቋሚ ቅ/ሲኖዶሱና እርሱን ለማጠናከር የተመረጡት ተጨማሪ ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት በተገኙበት በዛሬው ስብሰባ የዕርቀ ሰላም ልኡኩ ሪፖርቱን ማቅረቡ ተዘግቧል፡፡ የሰላምና አንድነት ጉባኤው ታኅሣሥ 12 ቀን 2005 ዓ.ም ያወጣውና የዕርቀ ሰላም ልኡኩ ተቃውሞታል የተባለው መግለጫም ውይይት ተካሂዶበታል ተብሏል፡፡ የሰላምና አንድነት ጉባኤው ‹‹ቅ/ሲኖዶሱን በመግለጫ ዘልፏል›› በሚል ማክረሪያ ነጥብ የዕርቀ ሰላም ጉባኤው ተስፋ እንደተሟጠጠ የሚገልጡ አቋሞች በመንበረ ፕትርክና አላሚዎች የተራመዱ ቢኾንም የዕርቀ ሰላም ሂደቱ አሁንም ቅድሚያ ትኩረት ተሰጥቶት በሌላ አነጋጋሪ አካል መቀጠል እንጂ መስተጓጎል የለበትም የሚለው የዕርቀ ሰላም ልኡካኑ ጠንካራ መከራከሪያ ተቀባይነት አግኝቶ አስቸኳዩ የምልአተ ጉባኤ ስብሰባ መጠራቱ ተገልጧል፡፡

በተያያዘ ዜና የሰላምና አንድነት ጉባኤው ልኡክ ሊቀ ካህናት ኀይለ ሥላሴ ዓለማየሁ ከአገር በግዳጅ እንዲወጡ ከተደረገ በኋላ በሀገር ቤት የቀሩት ሌላው ልኡክ መ/ር አንዱዓለም ዳግማዊ÷ ዛሬ ወደ መንበረ ፓትርያሪኩ እንዲገቡ ተፈቅዶላቸው ከዐቃቤ መንበረ ፓትርያሪኩ ብፁዕ አቡነ ናትናኤል ጋራ መወያየታቸው ተሰምቷል፡፡ የሰላምና አንድነት ጉባኤው አንዳንድ አባላት በሊቀ ካህናት ኀይለ ሥላሴ ዓለማየሁ ላይ በተወሰደው ርምጃ ምክንያት ‹‹እኛ ሂደቱን ከዚህ አድርሰናል፤ ጉባኤው በማንኛውም አደራዳሪ ቢተካም ከሥር ኾነን እንላላካለን›› ማለታቸው ተዘግቧል፡፡

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የሰላምና አንድነት ጉባኤ በአገር ውስጥና በውጭ በስደት በሚገኙት ብፁዓን አባቶች ዘንድ ዕውቅናና ተቀባይነት አግኝቶ ለቤተ ክርስቲያን ሰላምና አንድነት ሲሠራ የቆየ አካል መኾኑ ይታወሳል፡፡

Happy
Happy
0 %
Sad
Sad
0 %
Excited
Excited
0 %
Sleepy
Sleepy
0 %
Angry
Angry
0 %
Surprise
Surprise
0 %
    Print       Email
  • Published: 11 years ago on January 1, 2013
  • By:
  • Last Modified: January 1, 2013 @ 10:42 am
  • Filed Under: Ethiopia
  • Tagged With:

Average Rating

5 Star
0%
4 Star
0%
3 Star
0%
2 Star
0%
1 Star
0%
<"Without the support of our readers, the Maleda Times website would not exist in its present form">

You might also like...

በሰሜን ሸዋ ዞን ኤፍራታ እና ግድም ወረዳ መከላከያ ከአማራው ማህበረሰብ እና ከፋኖ ጋር ጦርነት ገጥሟል

Read More →

This site is protected by wp-copyrightpro.com

%d bloggers like this:
Skip to toolbar