www.maledatimes.com ኢትዮጵያ፡- ሃለፊነታቸውን የዘነጉት ግድ የለሽ ምሁራን (Alemayehu G. Mariam ) - MALEDA TIMES
Loading...
You are here:  Home  >  Ethiopia  >  Current Article

ኢትዮጵያ፡- ሃለፊነታቸውን የዘነጉት ግድ የለሽ ምሁራን (Alemayehu G. Mariam )

By   /   January 23, 2013  /   Comments Off on ኢትዮጵያ፡- ሃለፊነታቸውን የዘነጉት ግድ የለሽ ምሁራን (Alemayehu G. Mariam )

    Print       Email
0 0
Read Time:35 Minute, 40 Second

ከፕሮፌሰር ዓለማየሁ ገብረማርያም

ትርጉም ከነጻነት ለሃገሬ

በቅርቡ ናኦም ቺሞስኪ: የኤም አይ ቲ (M.I.T.) ዩኒቨርሲቲ የስነ ቋንቋ ፕሮፌሰርና የአሜሪካ ቀደምት ምሁር፤ ለአልጀዚራ ስለአሜሪካ የቀለም ሰዎችና ምሁራን በሰጡት ቃለ መጠይቅ ላይ ምሁሮቹ ሃላፊነት ጉድለትና ግድ የለሽነት አንደሚያሳዩ መግለጫ ሰጥተው ነበር፡፡ ላለፉት 4 አሰርት ዓመታት የ84 ዓመቱ ቺሞስኪ ተጋፍጠው ፤ ሃይላነ ጉልበተኞች ነን የሚሉትንም በሃቅ አለንጋ ሲሸነቁጣቸው ነበር፡፡ በቅርቡም የፕሬዜዳንት ኦባማን ደካማ ጎን አስመልክቶ ትችቱን ሲያሰሙ ፤ ፕሬዜዳንቱ ‹‹የዓለም አቀፍ የግድያ ዘመቻ ለመፈጸም›› የድሮን (ሰው አልባ አሮፕላን )ጦርነት አካሂደዋል›› በብለወ ነበር:: በሃቅኝነታቸው  ምክንያት ቺሞስኪ ‹‹ግራ ክንፈኛ›› ‹‹አክራሪ ፖለቲከኛ›› ከዚያም አልፎ ‹‹ኮሚኒስት›› በመባል ተኮንኗል፡፡ በርካታ ዋጋ ቢስ ቅጽል ስሞችም ተለጥፎባቸዋል፡፡ ያሻውን ቢባሉም  ተናጋሪው የዕድሜ ባለጸጋ ከቆሙበት ዓላማ ዝንፍ ሳይሉ፤ ያነሱትን ነጥብ ሳይለቁ ሳይስቱ  ተጠናክሮ እንደቀጠሉ ነው፡፡አሁንም ካታሊዝምን፤ ኒዎ ሊቤራሊዝምን፤ግሎባላይዜሽንን፤ጦር ሰባቂነትን፤ ሙስናን፤ ጭቆናን፤ ስልጣንን አለአግባብ መጠቀምንና በስልጣን መባለግን፤የሰብአዊ መብት መደፈርን፤በአሜሪካና በሌሎችም ሃገሮች ያለውን ሁኔታ ይተቻሉ፡፡ ከዚያ ባሻገር ደሞ የስነ ቋንቋ ምሁራዊ ተግባራቸዉን ከማከናወን ዝንፍ አላሉም ፡፡

‹‹ኖአም ቾምስኪ፡ የተሳካላቸው ሃላፊነት››፤ በሚል ለአልጄዚራ በሰጡትው ቃለ መጠይቅ፤ ቾምስኪ የአሜሪካንን ምሁራን ስልጣናቸውን መከታ በማድረግ  የዜጎችን ስልጣን ለመግፈፍና ግራ በማጋባት ወደ ግዑዝነት በመለወጥ፤ተለማማጭ በማድረግና መከታ በማሳጣት ረገድ ማሕበራዊ ሃላፊነት ማጣት፤ንፉግነት፤ዘራፊነታቸውን አስመልክቶ ተችቷል፡፡

አል ጀዚራ፡-በፖለቲካ ውስጥ መካተት የምሁራንና የሌሎችም አዋቂዎች ሃላፊነት ነው?

ቾምስኪ፡- ሰብአዊ ፍጡሮችን ሁሉ ያካትታል፡፡ ሃላፊነት እኮ በምቹ ጊዜ ላይ ነው የሚለካው፡፡ ድሃ ሰው ከሆንክና በዝቅተኛ ቦታዎች የምትኖር ከሆነ፤ ምግብህን ለማግኘት ብቻ በሳምንት 60 ሰአታት የምትለፋ ቢሆን፤የሃላፊነት ደረጃህ ከምታገኘው ጥቅም አኳያ የሚለካ ይሆናል፡፡

አልጀዚራ፡- የተሻሻለ ጠቀሜታ ካለህ በምላሹ የበለጠ እንድትሰጥ ትገደዳለህ?

ቾምሰኪ፡- ነውና፡፡ የበለጠ ተጠቃሚ ከሆንክ፤ የበለጠ ስለሚመችህ ያንኑ ያህል ማበርከት ይኖርብሃል፡፡ የበለጠ ተጠቃሚ ስትሆን ሃላፊነትህም ያንኑ ያህል ነው፡፡ ይህ እኮ በጣም ተራ ግልፀ ነገር ነው፡፡

አልጀዚራ፡- ይህን ሁኔታ ታዲያ ለምን በአሜሪካ አናየውም? ስለሰዎች በሃብት እየደረጁ መሄድ ብዙ ይሰማል፤ በርካቶችም ወደ ድህነቱ እየወረዱ ነው፤ያም ሆኖ በሃብት የደረጁትና ያካበቱት ጊዜያቸውን፤ከሃብታቸው፤ ከችሎታቸው ከጥቅማቸው አኳያ ሲያውሉ አይታዩም?

ቾምስኪ፡- እንደእውነቱ ከሆነ ሃባታሞች የሆኑት እኮ ለዚህ ነው፡፡ህይወትህን የምትመራው እራስህን ብቻ ለማበልጸግ ከሆነና ጥቅምህና ሃሳብህ ያ ከሆነና የሌሎች ችግር ካልታየህና ግድ የለሽ ከሆንክ፤ ስለሌሎች ማሰቢያ ሕሊናም አይኖርህም፡፡ ይህ ‹‹እራስ ወዳድነት ነው›› እንደሙት አካል መሆን ነው፡፡ ይሄ የአያን ራንድ ፍልስፍና ነው:- ‹‹ስለማንም ግድ የለንም፡፡ እኔ እራሴን ለማደርጀት ብቻ ነው የማስበው፤ያ ደሞ ክቡርና የተቀደሰ ተግባር ነው፡፡”

ዕውቁ ጋናዊ ኢኮኖሚስት እና በአፍሪካ ግንባር ቀደሙ ምሁር፤ ጆርጅ አይቴ በአፍሪካውያን ምሁራንና ዕውቀት የዘለቃቸው ታዋቂዎች ስላጡት የሃላፊነት ብቃት ቅሬታውን ከማሰማት አልቦዘነም፡፡ የአፍሪካ የምሁራን ክፍል ‹‹ከአፍሪካ ደም መጣጭ መሪዎች›› ጋር አንሶላ በመጋፈፍ ከመናጢውና ምስኪኑ ሕዝብ ላይ በመግፈፍ ኪሳቸውን ለመሙላት አሸሼ ገዳሜ ላይ ናቸው፡፡ በ1996 ለአፍሪካ ምሁራን ስለምንነታቸው ከምር የሚያምንበትን ነግሯቸዋል፡፡ “የፖለቲካ ሰዎች፤ የበቁ መምህራን፤ጠበቆች እና ሃኪሞች እራሳቸውን እንደሴተኛ አዳሪ በችሎታ ከነሱ አናሳ የሆኑትን ወታደራዊ ወሮበሎችን ፈላጭ  ቆራቾችን ላመገልገል እራሳቸውን አቅርበዋል፡፡ ደግመው ደጋግመው መልሰው መላልሰው እየተደፈሩ፤ ክብራቸው እየተገፈፈ፤ እየተሰደቡ፤ተሰልፈው ካገለገሉ በኋላ እንደቆሻሻ ጥራጊ ይጣላሉ—የባሰም ሊሆን ይችላል፡፡ እነዚህኞቹ ሲጠረጉና ሲጣሉ፤የበለጠ ክህሎት ያላቸው ምሁራን ሴተኛ አዳሪዎች በቦታቸው ለመተካት አንዱ በአንዱ ላይ በመጨፈላለቅ ይሽቀዳደማሉ›› ነበር ያሉት  አይቴ፡፡

የታደሉትና የተሟላላቸው ኢትዮጵያዊ  ምሁራን ሃላፊነት ማጣት

እና ታዲያ ለምንድንነው የኢትዮጵያን ምሁራን በፖለቲካው መስክ የማናያቸው? ምናልባት በአሜሪካን አቻዎቻቸው እግር በመተካት ላይ ይሆኑ? ወይስ የአያን ራንድ ፍልስፍና ተከታዮች ሆነው ይሆን? ‹‹ስለማንም ደንታ የለኝም፡፡ እኔ ስለራሴ ብቻ ነው ጭንቀቴ፤ያ ደሞ  የተቀደሰና ክቡር ምግባር ነው::›› የአይቴ ነቃፊ ትችት ለኢትዮጵያ ምሁራንም ይሰራ ይሆን?

በጁን 2010 አንድ ጥያቄ አንስቼ ነበር፡- ‹‹የኢትዮጵያን ምሁራን ምን በላቸው የት ገቡ?›› የሚል፡፡ በዚያን ወቅት መልስ አላገኘሁም ነበር::  አሁንም ምላሽ ባላገኝም ቀድሞም ሆነ አሁንም፤  ጉልህ በሆነው ከሕዝባዊ መድረኩ መጥፋታቸው ለረጅም ጊዜ ግራ ተጋብቻለሁ፡፡ ድርጊታቸው የጥንቱን ‹‹የግሪክ ፈላስፋ ዲዎጋንን፤ በጠራራ ጸሃይ ፋኖስ ይዞ ታማኝ ሰው ፍለጋ›› በአቴንስ ጎዳናዎች ላይ  የወጣውን አስታወሰኝ፡፡  ልክ እንደዲዎጋን፤ ዓለም አቀፎቹን የምእራቡን የምሁራን አምባ፤ የስነጥበብን የሳይንስ ሙያ ሰፈሮችን ገዳም መሰል መሸሸጊያዎችን፤ችቦ በመያዝ የኢትዮጵያን ምሁራን በየጉዳንጉዱ ሁሉ መፈለግ ያስፈልግ ይሆናል::›› ሆኖም  የትም ቢዳከር አልተገኙም፡፡ምናልባትም በማያሳይ ልዩ መጠቅለያ ተጀቧቡነው ተሰውረው ይሆን?

እውነቱን ለመናገር እኔም ለረጅም ጊዜ በዚያ የኢትዮጵያዊያን ምሁራን በተሸጎጡበት ያልታወቀ መደበቂያ ውስጥ ምንም ላለመተንፈስ፤ መስማት የተሳነኝ ድምጽ አልባም የሆንኩ ነበርኩ፡፡ ከዚህ የተሸፈንኩበት ዋሻ ለመውጣት ያበቃኝ የመለስ ዜናዊ ጦረኞች 196 ንጹሃን ዜጎችን እያነጣጠሩ ለሞት ሲዳርጓቸውና ከ800 በላይ የሚሆኑትን ሲያቆስሉ ማወቄ ነው፡፡ መቸም በሴቷም ሆነ በወንዱ ሕይወት ውስጥ አንድ ወሰኝ ወቅት አለን::  ከታፈንበት ማነቆና ዝምታን በመስበር በሰው ልጆች ላይ የሚፈጸመውን ኢሰብአዊነት፤ግድያ፤ ለማውገዝና ከተጎጂዎች ጋር ቆመን ለመጮህ የምንቆርጥበት፤ ክፉ ዘመንን አስወግደን ነጻነትን የምናመጣበትን ጊዜ የምናመቻች የምንሆንበት ወቅት ይመጣል፡፡ ላንዳንዶቻች  አንደዝዚህ ይሆናል::

ነገር ግን ትንፍሽ ላለማለት ለእራሳቸው ቃል ገብተው መኖርን፤ ምርጫቸው፤ የነቃ ሕሊናቸው፤ የወሰነላቸው በማድረግ የተሸሸጉ አሉ፡፡ምርጫ በጠራራ ጸሃይ ሲሰረቅ እያዩ በውቅታዊ መታወር መኖርን ምርጫቸው ለምን  አደረጉ? ለምንስ ንጹሃን ዜጎች በዘፈቀድ በደህንነት አባላት ሲያዙ፤ በእርባና ቢሱና ፍትሕ አልባ በሆነው ‹‹ችሎት›› ሲፈረድባቸው፤እየሰሙ ጆሮ ዳባ ልበስ ማለታቸውስ ለምን?  የዕምነት ነጻነት ሲደፈርና ሕብረተሰቡ ነጻነትን ሲማጸን እየመሰከሩ ለምንስ አብረው አልቆሙም አልወገኑም? ሕሊናቸውን በማጽናናትና በዝምታ በማማረር በማላዘን፤ በሰሙኝ አልሰሙኝ መቆጨት ምርጫቸው ለምን አደረጉ? በዝምታ ተሰውረው መኖር ነው ሕይወታቸው፡፡

ይህን መገንዘብ በጣም አስቸጋሪ ነው፡፡ ምናልባት ዝምታ ወርቅ ነው የተባለውን በማመን ይሆን? ወርቅ ከፈለግህ ዝም በል ማለት ነው? ጭቆናን የምያራዘመው ዝምታ አንደሆነ ዘነጉትን? ምናልባት ምናልባት፤ ዝምታቸው መሃይምናን እና ኋላቀር ብለው ለሚገምቷቸው፤ ስለሚያሰሙት ጩኸት ተቃውሟቸው ሆኖ ይሆን? ‹‹አረመኔያዊ የሆነው ውሸት በጸጥታ መገለጹን›› ቸል ብለውት ይሆን?  አረመኔያዊ ድርጊቶች በጸጥታ መታለፋቸውንስ? ይህ ስሜትን የሚነካ ተግባራቸው ‹‹ለማንም ደንታ የለኝም፡፡ እኔ ስለራሴ ብቻ ነው ጭንቀቴ፤ያ ደሞ  የተቀደሰና ክቡር ምግባር ነው›› የሚለውን የአያን ራንድን ፍልስፍና ተቀብለውት ይሆን?

ነገር ግን ዝምታ ወርቅ አይደለም፤ ዝምታ ገዳይ ነው፡፡ የጅርመን ምሁራን ናዚ ወደስልጣን መወጣታቱን በተመለከተ በዝምታ ሲዋጡ የታዘበው ናይሞለር ምሬቱን ሲገልጽ፡-

በቅድሚያ ኮሚኒስቶች ላይ አነጣጠሩ፤

የዚያን ጊዜ ኮሚኒስት ስላልነበርኩ ዝም አልኩ፤

ቀጥለው በሶሻሊስቶች ላይ አነጣጠሩ፤

የዚያን ጊዜ ሶሻሊስት ስላለነበርኩ ዝም አልኩ፤

ለጥቀው ወደ ሠራተኝው ማሕበር አነጣጠሩ፤

የዚያን ጊዜ የሠራተኛው ማሕበር አበል ስላለነበርኩ ዝም አልኩ፤

መጨረሻ ላይ ወደኔ መጡ፤

በዚያን ጊዜ ለኔ የሚጮህልኝ አንድም አልተረፈም ነበር፡፡

ዶክተር ማርቲን ሉተር ኪንግ ጁኒየር እንዳስጠነቀቁት፤ ‹‹በመጨረሻው የምናስታውሰው የጠላቶቻችንን ቃላትና ድርጊት ሳይሆን የወዳጆቻችንን ዝምታ ነው::››

የኢትዮጵያዊያንምሁራንማሕበራዊሃላፊነት?

የሕዝብ ድምጽ የዓምላክ ድምጽ ነው (vox populi, vox dei) ይባላል፡፡ ሆኖም ጸጥታ ከተጨቆኑ ጋር መነጋገርያ  መገናኛ ሊሆን አይችልም፡፡ ምሁሩ ለመናገር፤ለማሰብ፤ ለማወቅ፤ ለመፍጠር፤ በሃሳቡ ለማየት የታደለ ነው፡፡ ጸጥታ ዝምታ የተጨቋኞች፤ የተወነጀሉት፤ የተፈረደባቸው ከታደሉት አነስተኛው ሁኔታ ነው፡፡ ዝምታ የምስኪኖች፤ የአቅመቢሶች፤ መከላከያ አልባ ለሆኑት የመጨረሻው የችግርና የአማራጭ ማጣት የመኖራቸው ምርጫ ነው፡፡

ምሁራን በዝምታ ለታገዱት የመናገር የሞራል ግዴታና ሃላፊነት አለባቸው፡፡ በዝምታ ቆሞ ምንም ሳያደርጉ በችግር ጨኸት ስር ማጉረምረም ጨርሶ ምርጫቸው ሊሆን አይገባም፡፡ ለመማር፤ ለማሰብ፤ ለመጻፍ፤ ለመፍጠር የታደሉት፤ በቁሳቁስ እጦት ለተጎዱት ብቻ ሳይሆን ሰብአዊ ክብራቸው ለተገፈፈባቸውም ሕዝቦችም መልሰው መስጠት፤ መክፈል  መቻል አለባቸው፡፡

በዝምታ የተዋጡት የኢትዮጵያ ምሁራን የሳቱት አንድ ነገር አለ፡፡ ዝቅ ተደርገው ለሚታዩት፤ ለተናቁት፤ ድምጻቸው ለታፈነባቸው መናገር ጫና ሳይሆን መታደል ነው፡፡ ድምጽ አልባ ለሆኑት ድምጽ ለመሆን መብቃት የተለየ ክብርና ሞገስ ነው፡፡ ለገዢዎችና ለጉልበተኞች፤ ኃይል ያጡትን ወክሎ ዕውነትን ማሳወቅ፤ዋጋ የማይተለምለት ታላቅ ስጦታ ነው፡፡

ዝምተኛው ምሁር፡- የሞራል ግዴታውን በመርሳት፤ደስታውን ከማሳደድ ባሻገር፤ ከራስ ለማትረፍ ከመሯሯጥ ባለፈ፤ በፕሮግራም ታስሮና ተለጉሞ ከዚያ ውጪ የማይንቀሳቀስ የከፍተኛ ትምህርት ምሩቅ ግኡዝ ሮቦት ከመባል ውጪ ሊሆን አይችልም፡፡ በአንድ ወቅት ኒትዝኪ እንዳለው፤ ሁሉም ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት ‹‹ሰዎችን ወደ ማሺንነት የሚቀይሩ ተቋማት ናቸው›› በሱ ዘመን ሮቦት (በራሱ የሚንቀሳቀስ ተሽከርካሪ)አልተፈጠረም  ነበርና፡፡

በኔ እምነት ምሁራን የሞራል ዝግጁነት ሃላፊነት ሊኖራቸው ብቻ ሳይሆን፤ በተግባርም ሊወጡት ተገቢ ነው፡፡ ማለትም አንድ ሰው ለአንድ ዓላማ ሲቆም፤ ይህ ውሳኔው ከራሱ ጥቅምና ፍላጎት ባለፈ በርካታ መስዋእቶችን እንደሚያስከፍለው መረዳት አለበት፡፡ በርካታ ምሁራን ስለሰብአዊ መብት መደፈር የመቃወም ግዴታ እንዳለባቸው አበክረው ቃል ይገባሉ፤ በዚያ ጉዳይ ላይ ለመናገር ግን ዝግጁ አለያም ፍቃደኝነቱ በተግባር የላቸውም፡፡ በስልጣን የሚካሄድን ብልግና ለማጋለጥ አፋቸው አይደፍርም፡፡ ለመጻፍም ብዕራቸው ይዶለድማል፡፡ እርሳሳቸውም መቅረጫው ተሰብሯል፡፡ አንዳንዶች አይናፋር ናቸው፤ሌሎች ደሞ ድንበር የለሽ ፈሪዎች ናቸው፡፡ስለዚህም የሚናገሩት ድምጻ አልባ በሆነው ዝምታቸው ነው::

በ1967 ቾምስኪ ሲጽፉ  ‹‹የገዢዎችን ቅጥፈት ማጋለጥና እውነቱን ማሳወቅ የምሁራን ግዴታ ነው:: ተግባራቸውን  በመመርመር፤ ዓላማቸውንና ድብቅ እቅዳቸውን ይፋ ማድረግ…ለዕውነት መቆም የምሁራን ድርሻ ነው እንጂ ተከታዩን የነጻነትን ጥያቄ ለማጭበርበሪያነት እንዲጠቀሙበት መፍቀድ አይደለም::›› እንደኔ  እምነት የኢትዮጵያ ምሁራን ሊሸከሙት የሚገባቸውም ይህንኑ ነው፡፡ ሙግት መግጠም ያለባቸው በስልጣን ላይ ያሉት ጨቋኞች ጋር ብቻ ሳይሆን እርስ በርሳቸውም ነው፡፡ የኢትዮጵያን ሕብረተሰብ ስለገጠመው ሁኔታና ችግሮች የተሻለ አማራጭ ብርታትና አለኝታነታቸውን፤ የጠነከረ ተስፋ ማቅረብ ይገባቸዋል፡፡ አምባገነኖችን በአዳዲስና ጠንካራ አስተሳሰቦች  መዋጋት ከፍተኛ ግዴታቸው ነው፡፡ ታሪክ እንደሚያረጋግጠው ጊዜው የደረሰ ጠቃሚ ሃሳብ ጨርሶ ሊሸነፍ አይችልም፤ ሊገታም አይሞከረም፡፡

ኢንተርኔት በጭቆና ተግባሪዎችና በነጻነት ድል አድራጊዎች መሃል ያለውን ትግል አኩል ለማድረግ ችሏል፡፡ኢንተርኔት የቅሬታን ክረምት በመግፈፍ በመካከለኛው ምስራቅ ላሉ በሚሊዮን ለሚቆጥሩ የችግርና የመከራ ሰለባዎች፤ በጋውን የበለጸገ የነጻነት ወቅት በማድረግ እስካሁንም ሳይጠወልግ እንደቀጠለ ነው፡፡ ሙባረክ፤ ቤን አሊ፤ ጋዳፊ፤ ባግቦ፤ እና በርካታ  ሌሎችም በሕዘቦቻቸው ውስጥ ዘልቆ የገባውን የጭቆና ስርአት በነጸነት የመተካቱ ሃሳብ ጨርሶ በህልማቸውም ታይቷቸው አያውቅም፤ የሚታሰብም አልነበረም፡፡ የኢትዮጵያም ዲካታተር ጨቋኝ ማን አለብኝ ገዢዎች፤ ምንም እንኳን ጋዜጦችን፤ ቴሌቪዥንን፤ ኢንተርኔትን እንደገል ንብረታቸው ይዘው፤ በርካታ ለሕዝብና ለሃገር የሚጠቅም ተግባር ሊከናወንበት የሚችለውን ከሕዝቡ በታክስና በተለያየ መነሾ የሚሰበሰበውን ገንዘብ በማውጣት ከውጭ ዕውነት የሚያጋልጡትን መገናኛ ብዙሃን ለማፈን ቢያውሉም፤ዕውነትን ሳንሱር በማድረግ ሕዝቡ መስማት የሚፈልገውን እንዳይሰማ ለማገድ ቢፍጨረጨሩም፤ ሕዝቡ የሚፈልገውን ከማድመጥና ከማወቅ ሊያቆሙት አልሆነላቸውም፡፡ ይህ በገሃድ የሚታይ አዉንታ ነው:: በዚህም ኢትዮጵያዊያን ምርጫቸውን እያዳመጡና እየተገነዘቡ ናቸው፡፡ የኢትዮጵያ ምሁራን በዚህ የትም ባለው መገናኛ ላይ ድርሻቸውን ለመወጣት አልተቻላቸውም፡፡የዚህም ውጤት ወጣቱ ትውልድ ኢንተርኔትን ለርካሽ መዝናኛዎችና ለግሳንግስ ተረብ ሚዲያውን መጠቀሚያ ሊያደርገው ተገዷል፡፡

የኢትዮጵያ ምሁራን የሶሻል፤ፖለቲካዊና የሳይንሳዊ ለውጥ ግንባር ቀደም ሃላፊ መሆን አለባቸው፡፡ ይህን እያቆጠቀጠ ያለውን ሚዲያ፤ ለወጣቱ ትውልድ ትክክለኛውን እውቀት ለማስጨበጥና ሃገራቸው ላይ የተከመረውን መከራ መግፈፊያነት እንዲውል ማድረግ ገዴታቸው ነው፡፡ ወሳኙ ትንቅንቅ የወጣቱን አስተሳሰብና ልብ ለመያዝ መቻሉ ላይ ነው፡፡ ለዚህ ከዲክታተሮችና ከጨቋኞች ጋር ያለውን ግብግብ በድል ለመወጣት አስፈላጊውና ወሳኙ፤ ጠመንጃና ታንክ ሳይሆን አዲስና ሃሳብና ፈጠራ ነው፡፡ ለኢትዮጵያ ከዚህ በማነቆ ከያዛት አስከፊ ስርአትና እርባና ቢሶች የስርአቱ አጎብዳጆችና ባለስልጣናት ማነቆ ለመላቀቅ ያለው ወሳኝ አማራጭ፤ የኢትዮጵያ ፖለቲካ፤ኢኮኖሚ፤ ዕውቀት እስካልሆነና ምሁራኑም የመሪነት ሚናቸውን ለመወጣት እስክልተንቀሳቀሱ ድረስ፤ ከዚህ እራሱን በራሱ በመኮፈስ በዙፋኑ ላይ ከተከመረው ጨቋኝ ገዢ መላቀቂያው አስቸጋሪ ነው፡፡

የኢትዮጵያ ምሁራን መላ ችሎታቸውን ጉልበታቸውን ጊዜያቸውን በኢትዮጵያዊያን ወጣቶች ላይ ነው ማዋል ያለባቸው (በአቦሸማኔው ትውልድ ላይ):: አዳዲስ ጥልቅ ሃሳቦችን ለወጣቱ ትውልድ ነው መወርወር ያለባቸው፡፡ አዳዲስ ሃሳብን እንዲሞክሩትና በውጤቱ ሃይል ላይ እንዲጨምሩት፤ ሂሳዊ አስተሳሰቦችን በመዝራት እንዲያለሙት፤ ነጻ አስተሳሰብንና መጠያየቅን በውስጣቸው እንዲያስተላልፉ፤ ዘወትር በባለስልጣናት ገዢዎች ላይ ብቻ ሳይሆን፤ በምሁራኑም በራሳቸው ላይ ተጠራጣሪ እንዲሆኑ ማበረታታት፤ ጥላቻን፤ቡድናዊ ስሜትን፤መንጋ አስተሳሰብን መዋጋት ማስተማር፤እራሳቸውንና አስተሳሳባቸውን የሚመዝኑበት መሳሪያ አስታጥቋቸው፤ተጻራሪ አስተሳሰቦች በማስረጃ ተደግፈው አሳማኝ ከሆኑ፤ሃሳባቸውን እንዲቀይሩ አስተምሯቸው፤የቆዩ ችግሮችን በአዲስ አስተሳሰብና መፍትሔ እንዲያርሙት አመላክቷቸው፡፡ስህተት ሲሰሩ ስህተታቸውን አምነውና ተቀብለው ለመታረምና በስህተታቸውም ይቅርታ እንዲጠይቁ ዝግጁ አድርጓቸው፡፡ ለዕውነት እንዲቆሙ፤ለሰብአዊ መብት መከበር ጥብቅና እንዲቆሙ በማስተማር መሆን ያለባቸውን ትክክለኛ ሆኔታ ለመሆን እንዲችሉ መንገዱን ምሯቸው፡፡

በጁን 2010 ባቀረብኩት ጦማሬ ላይ የኢትዮጵያን ምሁራን ከተጨቆኑት ጋር እንዲወግኑ አሳስቤም ተማጥኘም ነበር፡፡ያን ከጻፍኩ በኋላ፤የኢትዮጵያ ምሁራን ዝምታ አደናቋሪ ነበር፡፡ ይህን መልዕክት ልብን በሚያደፋፍሩ ቃላቶች ብዘጋው ደስ ባለኝ ነበር፡፡ ግን የዚያን ጦማር የመዝግያ አስተሳሰቤን አሁንም የቅሬታ ስሜቴንና የጨለመ ተስፋዬን  እንደያዘ ሰለሆነ ደግመዋለሁ፡፡

አመልካች ጣቴ ወደሌሎች በጠቆመ ቁጥር፤ ቀሪዎቹ ሶስት ጣቶቼ ወደኔ እንደሚያመላክቱ ቢጨንቀኝም አውቀዋለሁ፡፡ ሁሉም ኢትዮጵያዊያን ምሁራን ወዴት እንደደረሱ አውቃለሁ:: በዓለም ማእዘናት ገሚሶች ያልተዘጉት ዓይኖቻቸው ሳይጨፈኑ፤በዝምታ ውስጥ ታግተዋል፡፡ የትም ይሁኑ የትም፤ ደጋገሜ በድፍረት ላስጠነቅቃቸው የምሻው፤ በመጨረሻው ወቅት የ‹አይቴ አጣብቂኝ› ጥያቄ ጋር መጋፈጥ አይቀሬ ነው፡፡ ወይ ለኢትዮጵያ መወገንን ምረጥ፤ አለያም ከጨቋኞችና ከአምባገነን አውሬ መሪዎች፤ አስገድደው ከሚደፍሩ፤ ስልጣናቸውን አለአግባብ ከሚጠቀሙ፤ እና ሃገሪቱን ከሚያረክሱት ጋር አልጋ ተካፈል ፡፡

*የተቶረገመው ጽሁፍ (translated from):

http://open.salon.com/blog/almariam/2013/01/20/ethiopia_the_irresponsibility_of_the_privileged

(ይህን ጦማር ለሌሎችም ያካፍሉ::) ካሁን በፊት የቀረቡ የጸሃፊው ጦማሮችን  ለማግኘት እዚህ ይጫኑ::

http://www.ecadforum.com/Amharic/archives/category/al-mariam-amharic

http://ethioforum.org/?cat=24

 

Happy
Happy
0 %
Sad
Sad
0 %
Excited
Excited
0 %
Sleepy
Sleepy
0 %
Angry
Angry
0 %
Surprise
Surprise
0 %
    Print       Email
  • Published: 11 years ago on January 23, 2013
  • By:
  • Last Modified: January 23, 2013 @ 12:16 am
  • Filed Under: Ethiopia
  • Tagged With:

Average Rating

5 Star
0%
4 Star
0%
3 Star
0%
2 Star
0%
1 Star
0%
<"Without the support of our readers, the Maleda Times website would not exist in its present form">

You might also like...

በሰሜን ሸዋ ዞን ኤፍራታ እና ግድም ወረዳ መከላከያ ከአማራው ማህበረሰብ እና ከፋኖ ጋር ጦርነት ገጥሟል

Read More →

This site is protected by wp-copyrightpro.com

%d bloggers like this:
Skip to toolbar