www.maledatimes.com የአንድ አገር ዜጋ ሰበአዊ መብቱ ካልተከበረለት የሁለት አገሮች ዲፕሎማሲያዊ መንገድ ይደፈርሳል ። - MALEDA TIMES
Loading...
You are here:  Home  >  Ethiopia  >  Current Article

የአንድ አገር ዜጋ ሰበአዊ መብቱ ካልተከበረለት የሁለት አገሮች ዲፕሎማሲያዊ መንገድ ይደፈርሳል ።

By   /   December 2, 2013  /   Comments Off on የአንድ አገር ዜጋ ሰበአዊ መብቱ ካልተከበረለት የሁለት አገሮች ዲፕሎማሲያዊ መንገድ ይደፈርሳል ።

    Print       Email
0 0
Read Time:12 Minute, 23 Second

ሃገራት ሃገር የሚሆኑት ዜጎች ተከባብረውና ጥቅማቸው ሳይጓደል፤ መብታቸው ሳይሸራረፍ፤ ግዴታቸውን አክብረውና
እየተወጡ ሲኖሩበት ነው፡፡ ምድረበዳም ቢሆን በሃገር ክልል ውስጥ ተከልሎ አስፈላጊ ሲሆን ዜጎችም ሆኑ ጎብኚዎች
አለያም ለሌላ ምርምርን የመሰሉ ተግባራት ለመፈጸም የሚሄዱበት በመሆኑ ሃገር ነው፡፡
ሃገራት ደሞ ዜጎችንና መብትና ግዴታቸውን በአግባቡና በሕገ መንግስታቸው ላይ በሰፈረው ድንጋጌ መሰረት
የሚያስተዳድሩትን ሕዝብ እራሱ የመረጣቸው መሪዎች እንዲያስተዳድሩት ውክልና ይሰጣል፡፡ ውክልናቸውን ሲያፋልሱና
በአግባቡ መወጣት ሲሳናቸው፤ አለያም ከሕዝብ ጥቅም የራሳቸውን፤ ከሃገር ሉአላዊነት የራሳቸውን በስልጣን መቆየት
ሲያስቀድሙ፤ ተአማኒነት አጉድለው ከሕዝቡ፤ ከሃገር ላይ ሲሰርቁ፤ ሲመዘብሩ፤ ሲያጭበረብሩ ደግሞ እንዳስቀመጣቸው
ያወርዳቸውና ሌሎች ይተካል አጥፊዎችንም እንደ የድርሻቸው በነጻ የፍትሕ መድረክ ቅጣታቸውን ያስወስናል፡፡
ሕዝብ ሳይመርጣቸው በመንግስት ግልበጣ፤ በነጻ አውጪ ስም፤ በጉልበትና በጦር ሃይል አጀብ ስልጣን ላይ የወጡት
ግን ከላይ እንደተጠቀሰው አወጣጣቸው በጉልበትና በማጭበርበር፤ የማይፈጸም ቃል በመግባትና በማታለል ስለሆነ
ማውረድም የሕዝብ መብት መሆኑ ይቀራል፡፡ ወታደሮቻቸውን መርጠው በስልጣን ጉቦ አስክረው፤ በሃብትና ንብረት
መደርጀት አደንዝዘውና ሕሊናቸውን ያስቷቸውና ወደ አውሬነት ለውጠዋቸው፤በራሳቸው ሳይሆነ በጌቶቻቸው ትእዛዝ
የሚመሩ፤ ሃገርና ሕዝብን ክደው የግለሰብ አገልጋይነታቸውን አክብረው የሚገሉ፤ የሚያስሩ፤የሚበድሉ ደም ተጠምተው
ደም የሚያፈሱ የመግደል ሱሰኞች ሆነው እየገደሉ ለመኖር ይፍጨረጨራሉ፡፡
ማን ነክቶን ጠመንጃው ጥይቱ በእጃችን፤ ማን ፈርዶብን ፍትሁ በቁጥጥራችን፤ ማን ጠይቆን ኦዲቱ በኛ ስር፤ ማንስ
ለምን ብሎን ምክር ቤቱ በመዳፋችን ስር በማለት አንኳንስ ለሃገርና ለሕዝብ ሊያስቡ ቀርቶ መኖሩን አንኳን
ማስታወስ እስኪሳናቸው አብጠው ጠግበው የሚይዙት የሚጨብጡት ይጠፋቸዋል፡፡
ያም ሆነ ይህ፤ ይህ ሁሉ ጥጋብ፤ ይህ ሁሉ ማን አለብኝነት፤ ዝም ያለው፤ የታገሰው፤ የህዝብ ቁጣ የፈነዳ እለት
መግቢያ ቀዳዳ ፍለጋ መኬዱ አይቀሬ ነው፡፡
አነሳሴ ይህን ለማለት አልነበረም፤ ግን በቴሌቪዥን ሃይለማርያም ደሳለኝ የተባለው ፎርጅድ ጠቅላይ ሚኒስትር ነኝ
ባዩ በሳኡዲ ስለተፈጸመው ግፍና መጠን የዘለለ በደል አስመልክቶ ከአንድ ጋዜጠኛ፤
ጋዜጠኛ/ ‹‹…….አሁን የተከሰተው ሁኔታ በኢትዮጵያና በሳውዲ ማሃል ያለውን ግንኙነት ያበላሸዋል ብለው ያስባሉ?
ብሎ ለጠየቀው የሰጠው መልስ ለሰውዬው የነበረኝን የወረደ አመለካከት የባሰ እንዲያዘቀዝቅ አድርጎብኛል፡፡
በተለያየ ወቅት ያየነውና የሰማነው ሁኔታ ሞልቷል፡፡ ሰውዬው ምናልባት አያወቁም ብሎ ከሆነ የማያውቀውና ማወቅም
የማይፈልገውና እንደተሞላ አሻንጉሊት የሚነዳው እሱ መሆኑን ሊገነዘበው ይገባል፡፡
አንድ ምሳሌ ልጥቀስ፡ አሜሪካ ሶማልያ ውስጥ አልቃይዳን አስመልክታ ወታደሮቿን አሰማርታ በነበረበት ጊዜ
ሶማሌያዊያን አሜሪካን ውጣ፤ ሃገራችን ልቀቅ ቢሉት አሻፈረኝ በማለቱ አንዱን ወታደር ገድለው አስከሬኑን ሜዳ
ለሜዳ እየጎተቱ ቪዲየ አንስተው ይፋ በማድረጋቸው የአሜሪካ ጦር ተነቅሎ ወጣ፡፡ መንገስት ያንን ኢሰብአዊ ድርጊት
ተመለከተና ጎመን በጤና ሕዝብ ያምጽብኛል ብሎ ጓዝ አስጠቅልሎ አስወጣ፡፡ ለዜጋው መገደል ተቆረቆረ፡፡ ሌሎችም
መጥቀስ ይቻላል፤ ግን ለነሃይለማርያምና ጌቶቹ ለማስረዳት መሞከር በድንጋይ ላይ ውሃ ማፍሰስ ነውና ጊዜ
አላጠፋም፡፡
አቶ መለስ ዜናዊ በተመሳሳይ ምስኪን ወታደሮቻቸውን ወደ ሶማሌ ካዘመቱ በኋላ አንድም የሞተ የለም ከማለትም
አልፈው የሞቱትን አስከሬን እንኳ ወደ ሃገር ገብቶ እንዲቀበር ለማድርግ አልተቸገሩም፡፡ መሞታቸውንም እስካሁን
ያልሰማ ቤተሰብ መኖሩ የታወቀ ነው፡፡ ይህንንም ለመሸፋፈን የሟቾች የወር ደምወዝ ለቤተሰቦቻቸው መከፈሉ
ቀጥሏል፡፡ አንድም አልሞተም በማለት ሞትን ሊክዱ ቢሞክሩም መኖሩን እራሳቸውን በመውሰድ አረጋገጠላቸው፡፡
እና ሃይለ ማርያምም ከመለስ በመማር፤ ለቀረበለት ጥያቄ ስመልስ
ሃይለማርያም፤/ ‹‹በዚህች ትንሽ ጉዳይ የሁለቱ ሃገራት ወዳጅነት ይፈርሳል ብሎ የሚያስብ ሰው ካለ በሁለቱ
ሃገራት መሃል ያለውን ግንኙነት ካለማወቅ ነው›› ነበር ያለው፡፡ አቤት እንዴት ያሳፍራል! እንኳን እኛ
ኢትዮጵያዊያን ሳውዲዎችም ቢሆኑ ይህን ሲሰሙ ያፍራሉ፡፡ ለወገኑ ያልሆነ እኛን ለማግባባትና የኛን መሬት ግዢ
ላለማጣት ለኛ ተሟገተ ብለው ያፍራሉ፡፡ ወገኑን የከዳ እኛንም ከመካድ አይመለስም ብለው ያሽሟጥጣሉ፡፡
ምን ማለት ነው? ወገኖች በግፍ ሲገደሉ፤ ሲገረፉ፤ ለእስር ሲዳረጉ፤ መከራ ስቃይ ሲቀበሉ ያን የፈጸመውን ሃገርና
መንግስት መጠየቅ፤ ወግ ያላቸው ሃገራት እንደሚያደርጉት የግንኙነት መበላሸት ቅድመ ማስጠንቀቂያ የሆነውን
የኤምባሲውን አባላት ደረጃ መቀነስ ሲገባ፤ ጭራሽ የዜጎችን ሞት እንደትንሽ ጉዳይ መቁጠር ምን አይነት ስብእና
ነው? ምን አይነት ስልጣንስ ነው? ለዚህ ነው እንዴ፤ ትንሽ ጉዳይ በመሆኑ ነው እንዴ ሰማያዊ ፓርቲ ለወገኖች
በመቆርቆር መብታቸው ይከበር ብሎ ሰላማዊ ሰልፍ ሲያስወጣ በተሰላፊ ወገን አክባሪዎችና የወገን ተቆርቋሪዎች ላይ
ሃይለማርያም ዱላና እስር እንግልት የፈረደባቸው፡፡
አቶ ሃይለማርያም፤ በስሙ ላይ የድንግል ማርያምን ስም አንግቦ፤ አጠራሩንም የኢትዮጵያ ጠቅላይ ሚኒስትር የአፍሪካ
ሕብረት ሊቀመንበርን ተሸክሞ፤ እንዲህ አይነት ሃላፊነት ያጣ አባባል በማለቱ የሞቱትን ቤተሰብና የኢትዮጵያንም
ሕዝብ በአጠቃላይ ላደረግሁት የአፍ ወለምታና በአስተሳሰብ ስንኩልነት ላደረግሁት ይቅር በሉኝ ብሎ መለመን
አለበት፡፡ ጉዳዩ ትንሽ አይደለም የዜጎች ሕይወት አልፏል አሁንም እያለፈ ነው፡፡ ታስረዋል እየታሰሩም ነው፡፡
ተደብድበዋል እየተደበደቡም ነውና ሕዝብ በሃገር ውስጥ ባሉት የሰውዲ ዜጎች ላይ ተመሳሳይ ድርጊት ከመውሰድ
ቢቆጠብም አልተኛምና ከወዲሁ ሃይለማርያም ደሳለኝና ከጀርባው አልንጋ ይዘው የሚነዱት ጌቶቹ ቢያስቡበትና
ተገቢውን ተግባር ቢፈጽሙ ይበጃል፡፡
እግዚአብሔር ኢትዮጵያንና ኢትዮጵያዊያንን ይጠብቅ!

Happy
Happy
0 %
Sad
Sad
0 %
Excited
Excited
0 %
Sleepy
Sleepy
0 %
Angry
Angry
0 %
Surprise
Surprise
0 %
    Print       Email
  • Published: 10 years ago on December 2, 2013
  • By:
  • Last Modified: December 2, 2013 @ 2:35 am
  • Filed Under: Ethiopia
  • Tagged With:

Average Rating

5 Star
0%
4 Star
0%
3 Star
0%
2 Star
0%
1 Star
0%
<"Without the support of our readers, the Maleda Times website would not exist in its present form">

You might also like...

በሰሜን ሸዋ ዞን ኤፍራታ እና ግድም ወረዳ መከላከያ ከአማራው ማህበረሰብ እና ከፋኖ ጋር ጦርነት ገጥሟል

Read More →

This site is protected by wp-copyrightpro.com

%d bloggers like this:
Skip to toolbar