www.maledatimes.com ጨፈቃ እንዳይባክን ዳዋውን ትተን ዐይጧን ብቻ እንምታ ግርማ በላይ ኢትዮጵያ፤ አዲስ አበባ - MALEDA TIMES
Loading...
You are here:  Home  >  Ethiopia  >  Current Article

ጨፈቃ እንዳይባክን ዳዋውን ትተን ዐይጧን ብቻ እንምታ ግርማ በላይ ኢትዮጵያ፤ አዲስ አበባ

By   /   October 24, 2013  /   Comments Off on ጨፈቃ እንዳይባክን ዳዋውን ትተን ዐይጧን ብቻ እንምታ ግርማ በላይ ኢትዮጵያ፤ አዲስ አበባ

    Print       Email
0 0
Read Time:89 Minute, 54 Second

(gb5214@gmail.com)

 

ባለፈው ሣምንት የሆነ ነገር ጽፌ በአንዳንድ የነጻ ሃሳብን ፍሰት በሚፈቅዱ ድረ-ገፆች ማስነበቤ ይታወሳል፡፡ ያ ጦማሬ በተቃውሞው ጎራ ተሰልፈው እየታገሉ ለሚገኙ የተወሰኑ አካላትና ለላንቲካውና ለመናጆነትም ቢሆን ለአንድ አካሄዱ ‹ያስፈራኝ› ግለሰብ የተላከ ነበር፡፡ መልስ ስጠብቅ አንድ ሣምንት ሆነኝ፡፡ ነገር ግን በድጋፍም በነቀፌታም በስድብም ጭምር ጥቂት ከማይባሉ ግለሰቦች በኢሜል ከተላከልኝ መልእክት በስተቀር ከጠየቅኋቸው አካላት ጭንቀቴን ተረድተው በተዛዋሪም ቢሆን ሊታደጉኝ አልሞከሩም፡፡

በመሠረቱ አሁን ላይ ሆኜ እውነቱን ለመናገር መልስ አገኛለሁ ብዬ አልጠበቅሁም – መጠበቅ እንደነበረብኝ ግን መናገር ነበረብኝ፤ ዲፕሎማሲው ያስገድደኛል፡፡ ይሁንና መልስ የማላገኝበትን ምክንያት እኔም ስለምረዳው በዚህ ብዙም አልከፋኝም፡፡ አንድ ትልቅ ሀገራዊ ድርጅት ወይም ተቋም ለእያንዳንዱ ዜጋ ጥያቄ መልስ እንዲሰጥ አይጠበቅበትም፡፡ የሚፈጥረው precedence (መሰል ድግግሞሽ ልበለው?) የድርጅቱን የሥራ ጊዜና የትኩረት አቅጣጫ ስለሚያባክንና ስለሚያዛባ እንደዚህ ዓይነቱ ነገር በተለይ በታዳጊ ሀገራት እንደማይበረታታ ይገመታል፡፡ ይህ ዓይነቱ ነገር በአወንታዊነት በግልጽ ተቀምጦ የሚገኘው በሃይማኖት መጻሕፍት በተለይም በክርስቶስ አስተምህሮ ነው፡፡ “መቶ በጎች ያሉት ሰው ከነዚያ በጎች አንዲቷ ብትጠፋው ዘጠና ዘጠኙን በዱር ትቶ የጠፋችዋን በግ ፍለጋ ወደዱር ይሄዳል፤ ባገኛትም ጊዜ ጎረቤቶቹን ሰብስቦ ‹የጠፋችዋ በጌ ተገኝታለችና ደስ ይበላችሁ› ይላቸዋል …” የሚለውን እናስብ፡፡ እንግዲህ ዓለምና ሃይማኖት፤ ሥጋና ነፍስ፣ … ለዬቅል በመሆናቸው እንኳንስ ፖለቲከኞች የሃይማኖት አባቶች ራሳቸው ለሥጋቸው አድረው የትሚናውን አሽቀንጥረው የጣሉትን ለወገንና ለሀገር የመቆርቆር ስሜት ከአንድ ተቋማዊ ኅልው መጠበቅ የሚቻል አልሆነም፡፡ የመነቋቆሪያውን ወስዶ የመተሳሰቢያውን ጊዜ በቶሎ እንዲያመጣው መጸለይ ነው፡፡

በሌላ በኩል የደረሱኝን የኢሜል መልእክቶች በመፍታትና በመግጠም ከነዚያ ውስጥ ይህኛው ወይም ያኛው ከምጠብቃቸው መልሶች ውስጥ ሊካተት ይችላል ብዬ እንዳልፈርድ ልኮነንባቸው ሆነ፡፡ የግለሰቦችን ስሜት-ወለድ ፅብረቃዎች(reflections) እንደ ህገኛ መልስ መውሰድ ተገቢ እንዳልሆነ መገንዘብ አላቃተኝም፡፡ ብዙ መማር እንደሚቻልባቸው ግን ተረድቻለሁ፡፡ “አፍ ሲከፈት ጭንቅላት ይታያል” እንዲሉ ከነዚህ አጠገባቸው የሚገኝን ምናባዊ ጦር ሁሉ አንድም ሳያስቀሩ የወረወሩ ከሚመስሉ አስተያየተኞች ብዙ ነገር ተምሬያለሁ፤ ዱሮውንም ለመማር ነበርና መጻፌ፡፡ ወደዝርዝር ቢገባ አውሎ ያሳድራል፡፡

ነገር ግን ስለነዚህ ተሳዳቢ ኢሜሎች በደፈናው በጣም ጥቂት ነገር ማለት እፈልጋለሁ፡፡ ለሚፈልግ መማማሪያ ይሆናሉ፡፡

በውቡ ሥነ ቃላችን “በቅሎ አባትሽ ማን ነው?” ቢሏት “እናቴ ፈረስ ነች!” አለች ይባላል – የጨነቀ ነገር ቢገጥማት መሆን አለበት፡፡ ራስን ሆኖ የመገኘት ጣጣው ብዙ ነው፤ መሆን በምትፈልገውና በማትፈልገው መካከል ክፍተት ሲፈጠርብህና ማጣፊያው ሲያጥርብህ ወደላይ ወደኅሊናህ ሳይሆን ወደታች ወደጉልበትህ ወርደህ ትሸጎጣለህ – ላያዋጣ፡፡ ቀጥተኛው መልስ መሆን የነበረበት “ኦ! አባቴማ (ስናር?) አህያ ነው፡፡” የሚለው ነበር፡፡ ግን አፈረችበት፡፡ የተፈጠረችበትን ከዳች፡፡ እናም መልስ እያላት መልስ አጣች፡፡ እውነቱን ተናግራ እመሸበት ማደርን አልወደደችውምና ትዝብትን ወረሰች፡፡

ለማስረገጥ ያህል ሌላም አንድ ልጨምር፡፡

ጠያቂ፡-  “እንካስላንትያ በብጣሽ!”

ተጠያቂ፡- “ምን አለ በድሪቶ!”

የዚህ ባህላዊ ጨዋታ ምላሽ መሆን የነበረበት “ምን አለ በብጣሽ” ነው እንጂ “ምን አለ በድሪቶ” ከተባለ ተጠያቂው ሆን ብሎ ጠያቂን ለማደናገርና ጨዋታ ለማስቀየር አስቧል ማለት ነው፡፡ “ብጣሽ” ከሚጠበቀው “rhyme/rhythm” ከወጣ ጨዋታው ይበላሻል፡፡ በሸርና በተንኮል የተተበተበውን ፖለቲካዊ ባህላችንን በቅጡ የሚገነዘብ ዜጋ ምን እያልኩ እንደሆነ በደንብ ይገነዘባል ብዬ አምናለሁ፡፡

ጭንቀቴን በቀጥታ ተረድቶ የሚያጽናናኝን ነገር እንደመላክ የሰለቸኝን አታካሮና በ‹ቬና ኮንቬንሽን የተወገዘና በሕግ የተከለከለ› ኒዩክሌር-ቀመስ ሥራየቤታዊ ውርጅብኝ  ያስወነጨፉብኝን ሰዎች ስመለከት በእውነቱ በኢትዮጵያዊነቴ አፈርኩ፡፡ የፈጠጠን እውነት ተናግሮ እንዲገባኝ እርዱኝ ማለት በወያኔነት ማስፈረጅ ነበረበትን? ሥጋትን መግለጽ በብዕር ስም ከመጻፍና ካለመጻፍ ጋርስ ምን አገናኘው? ስሜ የብዕር ስም መሆኑንስ ተናገርኩ ወይ? “ግርማ በላይ” ‹የኮራ የደራ› ኢትዮጵያዊ ስም አይደለምን – እንኳን ይህንን “ወርቅ” ስምና “ግርፋት በዛብኝ” ተብዬ እንደጠራ ብፈልግስ ማን ነው እሚከለክለኝ? – ደግሞ ለሞላ ስም፡፡ ወይንስ ስልክ ቁጥሬን፣ ከፍተኛየን፣ ቀበሌየንና የቤት ቁጥሬን ጨምሬ መጻፍ ነበረብኝ? የሚገርም ነገር ነው፡፡ ጥያቄየ አሁንም እንደጥያቄ የሚሊዮኖች በመሆኑ ‹ግርማ በላይ›ነቴ አስፈላጊ ከሆነ ከቁብ አይጣፍና ይህ ጥያቄ ለእንደኔ መሰል በርካታ ተጨናቂዎች በአግባቡ ይመለስ፡፡ ችግሩ የአንድ ግለሰብ አይደለም፤ ችግሩ የዚህ ግለሰብ ስምም ሆነ አድራሻም አይደለም፤ አሁንም ችግሩ የዚህ ሰውዬ ደደብነትም ሆነ ሌሎች በአሥራዎች የሚገመቱ የዚህን ሰው ሞራል ድባቅ ለመምታት የሚለጠፉ ቅጽሎች ከዬአቅጣጫው መጉረፍ አይደለም፡፡ ችግሩ ዋናውን ጉዳይ ወደጎን እየተው በዘርፍ በዘርፉ ብቻ መረን በለቀቀ የቋንቋ አጠቃቀም በቃላት የጨበጣ ውጊያ መጠዛጠዙ አይደለም፡፡ የችግራችን ማዕከልና ለመፍትሔውም ሁላችን መረባረብ የሚገባን፣ ከመንደር አሉቧልታና አሰልቺ ከሆነ የገለማ እንካስላንትያ ዛሬውኑ ራሳችንን ነጻ አውጥተን  በብሩኅ ኅሊና ለሁሉም የሚበጅ መፍትሔ መሻት የሚኖርብን ሀገርን ከዳግመኛ ጥቃት መከላከሉ ላይ ነው፡፡ ይህ ደግሞ በግድ በጠበንጃ (ብቻ) መሆን የለበትም፡፡ በመሠረቱ ቢጨንቅ እንጂ ጠበንጃ የሰውነት ሳይሆን የእንስሳነት ባሕርይ መገለጫ ነው፡፡ስድብና ቁጣም፣ ዘለፋና ዛቻም እንዲሁ፡፡ ጠበንጃ በምንም ዓይነት መንገድ ጥሩ አማራጭ አይሆንም ፤ እርሱ ራሱ ጭንቅላት ስለሌለው ብቻ ሣይሆን ብዙውን ጊዜ ጠበንጃን የሚይዙት ሰዎች የጭንቅላታቸው ጤንነት ስለሚያጠራጥር ነው – በተለይ በሀገራችን፡፡ አማራጭ ይሁን ቢባልም እንኳን ዳፋው ብዙ ነው፡፡ ይህንን ስል ደግሞ ሼክስፒር ብሎታል ሲባል እንደሰማሁት “To do a great right, do a little wrong.” በሚለውና ቅዱስ ዳዊት በወጣትነት ዕድሜው በእግዚአብሔር ረድኤት ጎልያድን በወንጭፍ ድንጋይ መግደሉን፣ ሳምሶንም እንዲሁ ከፈጣሪው በተሰጠው ኃይልና ብርታት በአህያ መንጋጋ ከሦስት መቶ በላይ የጠላት ሠራዊትን መፍጀቱን እዘነጋለሁ ማለት አይደለም፡፡ እንዴትና መቼ መጠቀም እንዳለብን ካወቅን ነጻነትን በልመና ብቻ ለማግኘት ለሺዎች ዓመታት ደጅ ከመጥናት ይልቅ የተቀደሰ ኃይልን መጠቀሙ ጥፋት እንዳልሆነ እረዳለሁ – የተቀደሰ ኃይል መኖሩ እስከታመነበት ድረስ፡፡ ችግሬ ታዲያ ሌላ መሆኑን ልብ ይሏል፡፡ እንደምርጫ ከታዬ ግን ኃይልን መጠቀም የመጨረሻውና ሁሉም ተስፋ ሲመነምን መሆን አለበት – በአልሞትባይ ተጋዳይነት፡፡ እኔ ደግሞ ወያኔ ካለው የአውሬነትና የዘረኝነት ጠባዩ አኳያ ካለኃይል ሥልጣን የማይለቅ መሆኑን መቶ በመቶ አምናለሁ፡፡ እነጋንዲና ማንዴላ በሰላማዊ መንገድ የታገሉት እንደሰው ከሚያስቡ ፍጡራን ጋር እንጂ እንደወያኔ ካሉ ደመ ሞቃት እንስሳት ጋር አልነበረም፡፡ ከዚህ አንጻር ብረት ለምን አነሳ ብለን ማንንም መውቀስ ያለብን አይመስለኝም፡፡

ተቃዋሚም ሆነ ሌላ የመንግሥትን ሥልጣን ለመያዝ የሚያልም ተስፈኛ መጠንቀቅ ያለበትን ነገር ከወዲሁ መጠቆም አግባብነት አለው፡፡ ዛሬ ባለችው መሣሪያ ያልተገራ አንደበቱን ተጠቅሞ ሰዎችን የሚሳደብና በአፍ ጂዶ ቁጭ ቁጢጥ የሚያደርግ ሰው ነገ የሥልጣንን ኮርቻ ሲቆናጠጥ ዜጎችን በመትረየስ አስሰልፎ እንደማይረፈርፍ ምንም ዋስትና የለንም፡፡ ዛሬ ቤቱን ሲያንኳኩ ጆሮው እየሰማ በትዕቢት ተነፍቶ ለአንኳኪው ቀና መልስ የማይሠጥና ትህትና የሚጎድለው ነገ ወንበር ሲይዝ ምን ሊያሳይ እንደሚችል ከግምት ባለፈ ብዙ ማለት ይቻላል፡፡ ለክፉም ለደጉም ነቃ ማለት ደግ ነው፡፡ ለነገሩ ይህ ለአሁኑ የቅድሚያ ቅድሚያ የምንሰጠው ችግራችን አይደለም፡፡ ችግሩ ግን ችግር ነው፤ ሊያውም በተመሳሳይ አረንቋ የሚያርመጠምጥ ትልቅ ችግር፡፡ እናም ቢያንስ ዝምታም አንዳንዴ ወርቅ መሆኑን መረዳት ይገባል፡፡ ንፋስ ለሚያጮኸው ቆርቆሮ ሁሉ እየተነሱ በተመሳሳይ ድምፀት መጮህ ለትዝብት ይዳርጋልና አደብ መግዛቱ አይከፋም፡፡ እኔስ ከእውነት ቸግሮኝ ነው – በዚህ ዓይነት ሆን ብሎ ሊያስጮህ የሚዳዳው “እስኪ የትግስታቸውን ልኬት ልወቀው” የሚልም ሊኖር ይችላል እኮ፡፡

መልካም ነው፡፡ የምለው ወደምንምነት ይተርጎም ከመናገር ግን አልከለከልም፡፡ እናም እናገራለሁ፡፡ ሰሚ ይኑር አይኑር ያ ሁለተኛ ችግሬ ነው፡፡ የሚሰማ ይስማ፤ የማይሰማም የታወቀ ነው አይሰማም፡፡ ሀገራችን ትልቅ መንታ መንገድ ላይ ናት፡፡

ከትልልቆቹ ችግሮቻችን መካከል አንዱ መግባባት አለመቻላችንና አንዳችን አንዳችንን በከንቱ መፈረጃችን ነው፡፡ በሃሳብ የማትስማማውን ሰው ዘልለህ ስም መለጠፍ የሀገራችን ብቸኛ መለያ ሆኗል፡፡ ቆም ብሎ “ አሃ፣ ይሄ ሰው የሚለው ነገር አንዳች እውነት ይኖረው ይሆን እንዴ?” ብሎ ማሰብ የሚያስቀጣ ወንጀል የሆነ ያህል ነው፡፡ ይህ ህመም ደግሞ ከሞላ ጎደል የሁላችንም ህመም ነው፡፡ ተማረ አልተማረ መደማመጥ ብሎ ነገር ብዙም አይታይበትም፡፡ በዚህ ረገድ ፈረንጆች ያስቀኑኛል፡፡ በየትኛውም ደረጃ የሚያካሂዷቸውን ስብሰባዎች ስንታዘብ በዱላ ቀረሽ ንትርክ አልፎ አልፎም በቡጢ ሳይቀር( ይህን ባንወደውም) እየተቧቀሱ ተመልሰው ግን አብረው ይጫወታሉ፤ አብረው ይበላሉ፤ አብረው ይጠጣሉ፡፡ ቂም በቀል ብሎ ነገር የለም፤ ቢያንስ በዚህ ረገድ አእምሯቸውን ከአውሬነት ደረጃ አውጥተዋል ማለት ነውና ሊወደሱ ይገባቸዋል፡፡ እንዲያ ያወዛገባቸውና እስከቡጢ ያደረሳቸው ጉዳይ አንድ የጋራ ዓላማ መሆኑን ስለሚረዱ ጉዳዩ በድምጽም ይሁን በተለዬ ውሳኔ ዕልባት ካገኘ በኋላ የኋሊት ዞረው እንደአበሻ በ“ና ይዋጣልን!” የጅላጅሎች ፈሊጥ ጊዜያቸውን አያጠፉም፡፡ ሕይወት ወደፊት እንጂ ወደኋላ እንደማትራመድ ያውቃሉና በአሥርና በሠላሣ ዓመታት የጥንት ጠብ የዛሬን ደስታቸውን አያጠይሙም፡፡ እኛ ግን ሥጋችን በ21ኛው መቶ ክፍለ ዘመን እየኖረ መንፈሳችን ከብዙዎች ዓመታት በፊት በሚገኝ መቼት ውስጥ ተተብትቦ ይገኛል፤ መውጫ ቀዳዳ እንፈልግ፡፡ ይህ ነገር ቅስምን የሚሰብር የማንነታችን ነፀብራቅ ነውና ካለፈው እንማር፡፡ …

“ትኩስ ሬሣ የከረመውን ያስነሳ” እንደተባለው ሆኖብኝ ግራ ቀኙን እረግጥ ገባሁ እንጂ የነገሬ መነሾ ተስፋዬ ገ/አብ መሆኑ እንዳይዘነጋብኝ እፈልጋለሁ፡፡ ባያድለንና ባያድለው እንጂ ይህ ሰው ኢትዮጵያዊ ነበር – እሱ በሚለው መልክ ሳይሆን የጋራ ታሪካችን በሚያውቀው መንገድ፡፡ ኢትዮጵያዊነት ደግሞ ወደው የሚቀበሉትና የሚሞቱለትም እንጂ እንደተስፋዬ የጭቃ ውስጥ እሾህ እየሆኑ ለሀገሪቱ ውድመትና ከዓለም ካርታ ጨርሶውን መሠረዝ ሌት ከቀን የሚደክሙበት አይደለም፡፡ ተስፋዬ ይህችን ሀገር ለማጥፋት እንዲህ ሌት ከቀን የሚደክመው ከማን ተልኮ እንደሆነ የማያውቅ ቢኖር ማወቅ የማይፈልግ ብቻ ነው፡፡ ይህች ሀገር “በትውልድ እንግሊዛዊ በምርጫ ግን ኢትዮጵያዊ ነኝ” ብለው ፈረንጆች ሣይቀሩ በኩራት የተናገሩላትና አሁንም ድረስ ብዙዎች የሚናገሩላት የሚመኟትም ቆንጆ ሀገር ናት – (የሪቻርድ ፓንክረስትን ቤተሰብ ማስታወሴ ነው)፡፡ ወደፊትም ይህ ክብሯ ይመለሳል – ነገር ካልበዛብኝ በመጨረሻው አካባቢ የሚታየኝን እናገራለሁ፡፡ ይህን የሚያስቀና ክብሯንና ሞገሷን ለማጥፋት ሻዕቢያና ወያኔ መነሳታቸውን የሚረሳ የለም፡፡ በዚህ አስበርጋጊ ሁኔታ የምንደነግጥ ዜጎችን ማስታመም ሲገባ ይበልጥ ማስበርገግ አይገባም፡፡ የሚያስበረግግማ እዚሁስ መች አጣንና፡፡ ይሄን ነገር በነጥብ በነጥብ እንደመጣልኝ ካላስቀመጥኩት በጣም ሊንዛዛብኝ ነው፡፡

 

  1. ተስፋዬ ገብረአብ  ኢትዮጵያን እያጠፋ ሳለ ለኢትዮጵያ ነጻነት ከቆሙ ኃይላት ጋር ተባብሮ በመሥራት ላይ እንደሚገኝ በስፋት እዬተነገረ ነው፡፡ ይህ እንዴት ሊሆን እንደሚችል መጠየቅ ተገቢ ነው – አለመጠየቅ ነው እንግዲያውስ ፀረ-ኢትዮጵያ ሊያስብል የሚገባው፡፡ “የራስጌ ወለባ ያንገት ሀብል ናቸው” ካላላችሁኝ ተስፋዬና የኢትዮጵያ ነጻነት ምንና ምን ናቸው? ወይንስ አዲሲቷ ኢትዮጵያ አማራን አትጨምርም ማለት ይሆን? እንዲያ ከሆነ ቁርጡ ይነገረንና አማራን ከወያኔ በኋላ ሊገጥመው ከሚችል አደጋ ለመታደግ በቻልነው ሁሉ ቢያንስ እንጩህ፡፡ “ባለቤት ካልጮኸ ጎረቤት  አይረዳም”ና፡፡
  2. የኢሳይያስ አፈወርቂ ኤርትራ በምን ሁኔታ እንደምትገኝ ለማወቅ በግድ የኤርትራ ተወላጅ መሆንን አይጠይቅም፡፡ ሰሞኑን በታተመችው ‹ፋክት› መጽሔት ላይ እንዳነበብኩት ከመንግሥትነት ተራ ለመውጣት አንድ ሐሙስ እንደቀራት በአንድ ምሁር ጥናት መዘገቡን ተረድቻለሁ፡፡ በድህነት ሠንጠረዥ ከእኛም ሳታንስ አትቀርም፡፡ ይህች ልትፈራርስ የደረሰች ሀገር በምን ስሌት ይሆን የ80 እና 90 ሚሊዮን ሕዝብ ነጻነት ራሽን ልታድለን የተነሳችው? ነጻነት የቀበሌ መኮረኒና ፓስታ የሚገዛበት ኩፖን መሆኑ ነው እንዴ? አዎ፣ እናገራለሁ ብያለሁና — የሚያስጨንቀኝን ሁሉ እናገራለሁ፡፡
  3. የኤርትራ ሕዝብ አንድም ነጻነት የለውም፡፡ የታፈነ ሕዝብ ነው፤ እንደኛው በድህነት የሚማቅቅም ሕዝብ ነው፡፡ ዴሞክራሲን ቃሉንም እንኳን ሰምቶት አያውቅ እየተባለ እስከመቀለድ ተደርሷል፡፡ እኛስ ሊያውም ብዙ ወጪ እየተከሰከሰበት በትያትር መልክ በየአምስት ዓመት ወያኔ ከራሱ ጋር ተወዳድሮ ራሱ ሲያሽንፍና የዴሞክራሲ ስም ሲጠራ እንሰማለን፡፡ በዚህ ‹መንግሥት› ሥር ተጠልሎ እንዴት ነው ታዲያ … ጥበበ ወርቅዬ “አልገባኝም ገና…” ብሎ አቀንቅኗል ልበል?
  4. ቀደም ሲል ጥቁር ጫካ በሚል ስም በተጻፈ አንድ ረጂም ጽሑፍ ብዙ ነገር ተገንዝበናል -  ብዘዎቻችንን ‹አበላሽቶናል› ማለት ይቻላል፡፡ በዚያ ጽሑፍ ኢትዮጵያውያን ታጋዮች እንዴት ሻዕቢያ እንደተጫወተባቸው፣ እንዳሰራቸው፣ እንደገደላቸው፣ እንዳፈናቸው፣ እንደሰወራቸው… ብዙ ራስን የሚያዞር የሻዕቢያ ሤራና ተንኮል ተጠቅሷል፡፡ በዚያ በኩል ብዙ ሙከራ ተደርጎ እንደከሸፈ በበኩሌ አስታውሳለሁ – “እባብን ያዬ በልጥ በረዬ”፡፡ ለምሳሌ ቱጃሩ አቶ ያለምዘውድ አሁን ድምጻቸውም የለም፤ በዚያ በኩል ሊመጡ ወደዚያ ሄደው ነበር፡፡ ዛሬ እንዴት ሊሆንልን እንደሚችል ሳስበው እየጨነቀኝ ጠየቅሁ፡፡ ምናለበት ብጠይቅ? ደደብና አላዋቂ ሲጠይቅ በግለሰብ ደረጃም ቢሆን እንደርሱው ደደብና አላዋቂ መሆን ይገባ ነበርን? ባይሆን “የከረሜላ እናት ሞታለች!” ዓይነት ለሕጻናት የሚሰጥ መልስ ቢሰጠኝ እኮ ደስ ብሎኝ አርፌ እቀመጥ ነበር፡፡
  5. የመቶ ዓመት የቤት ሥራ እንደተሰጠን አውቃለሁ፡፡ ይህን ያወቅሁት ሰው ነግሮኝ ሣይሆን የዛሬ 23 ዓመታት ገደማ ወያኔ አዲስ አበባን ሻዕቢያ ደግሞ አሥመራን ሊቆጣጠሩ ዳር ዳር እያሉ በነበረበት ወቅት አቶ ኢሳይያስ ለአንድ የእንግሊዝ ታዋቂ መጽሔት በሰጡት ቃለ ምልልስ ነው፡፡ በዚያ ቃለ ምልልስ እንደገለጡት “የኤርትራን ነጻነት ማግኘት በጣም ቀላል ነው፡፡ ችግሩ ነጻነቱን እስከወዲያኛው ማቆየቱ ላይ ነው፡፡ ይህንንም ከሕወሓት ጋር በቅርበት እየተነጋገርንበትና ቀጣይነት ባለው ሁኔታ እየሠራንበት ነው፡፡” ብለው ነበር፤ ጊዜው በመራቁ ቃል በቃል አልጠቀስኩት ይሆናልና ይቅርታ፡፡ የመቶ ዓመቱ የቤት ሥራ በምዕራፍና በንዑስ ምዕራፎች በርዕሶችም ተከፋፍሎና በመልክ በመልክ ተሰድሮ አላየነውም፡፡ ነገር ግን እስካሁን ካየናቸው ሁኔታዎች መረዳት እንደሚቻለው የቤት ሥራው በተገቢው መንገድና እንደታቀደው እየተካሄደ እንደሆነ ጡት ያልጣለ ሕጻንም ይረዳዋል፡፡ የሰሞኑ ግርግር ቢያስደነግጠኝና እንደ አንድ ዜጋ ማብራሪያ ብጠይቅ ታዲያ ምኑ ላይ ነው ጥፋቱ? ለነገዬ የሚጨነቁልኝ ከመኖራቸው ጎን ለሆን እኔስ ለራሴ ብጨነቅ ምን ክፋት አለው?
  6. ለመሆኑ እንኮሎኔል ታደሰና ሌሎችም በምድረ ኤርትራ እስር ቤቶች የታጎሩት የሚቆረቆርላቸው መንግሥት አልባ ኢትዮጵያውያን ለምን እንደታሰሩ ቀሩ? ኮሎኔል በዛብህ ለምን ደብዛው ጠፍቶ ቀረ? በቅርብ አቦይ ስብሃት ተናገሩ የተባለው እውነት ከሆነም ለምን ተገደለ? በየትኛው ሀገር ነው የጦር ምርኮኛ – ከአሥር ተከታታይ ጊዜያት በላይም እንኳን ቢማረክ – በዘፈቀደ የሚገደለው? በትግሉ ዘመን በተለይ አማሮች የሻዕቢያ ጦረኞች የዒላማ መለማመጃ እንደነበሩ መነገሩን ሥራቸው ያውጣቸው፣ እነሱው ይኮነኑበት ብለን ልንረሳው ብንሞክርም፣ “አሥር አማሮች በግድግዳ ላይ፣ ድንገት አሥሩም ወርደው ቢከሰከሱ ስንት ይቀራሉ?” በሚል የሰብኣዊነትን ጠርዝ የለቀቀ የጥላቻ ማስፋፊያ መንገድ የሻዕቢያ ሕጻናት የሒሳብ ትምህርት ይማሩ እንደነበር የተሰማውን ነገር የጠላት ወሬ ነው ብለን ብንተወው፣ … እንዴት አሁን በቅርብ ይህን ከፍ ሲል የተገለጸውን የመሰለ የክፋት ሥራ በ”ጎረቤት” ሕዝብና ሀገር ላይ ይሠራል? ሶማሊያ እንኳን ከ11  ዓመት እሥር በኋላ አብራሪ ኮ/ል ለገሠን መልሳልን የለምን? የኛዋ የዛሬው የነጻነት አርበኛ ኤርትራ እንዴት ከሶማሊያ ልታንስ ቻለች? አንድ የሰው ራስ እንዴት ሁለት ምላሶችን ሊይዝ ይችላል?  ለመሆኑ አቶ ኢሳይያስ ስንት ናቸው? የኤርትራስ መንግሥት?
  7. አቶ ኢሳይያስ በቅርቡ የኢትዮጵያን ዕድሜ ወደ 65 ዓመት ገደማ እንዳወረዱት አንብቤያለሁ፡፡ “የበላችው ያስገሳታል፤ በላይ በላዩ ያጎርሳታል፡፡” እንደምንለው የወያኔው የመቶ ዓመት ዕድሜያችን ተነግሮልን ተደምመን ከማብቃታችን ዛሬ ደግሞ የነጻነታችን ዋልታና መከታ ብፃይ ኢሳይያስ ወደ 65 አወረዱን፡፡ ይህ ምን አንድምታ አለው? ማን ነው ማንን የሚያታልለው?[አንድ የሰማሁትን ቀልድ ልንገራችሁ፡- አንድ መምህር ብላክቦርድ ላይ አንዲት ጦጣ ይስልና “ተማሪዎች፣ የዚህች ጦጣ ጅራት ርዝመት ስንት ይሆናል?” ብሎ ይጠይቃል አሉ፡፡ ተማሪዎቹም እጃቸውን እያነሱ አንዳቸው አንድ ሜትር፣ ሌላኛቸው ሃምሳ ሣንቲም … እያሉ እያሉ ይወርዱና የመጨረሻው ልጅ እጁን አንስቶ “ቲቸር፣ በኔ ግምት አምስት ሣንቲ ሜትር የሚረዝም ይመስለኛል” ይላል፡፡ ይሄኔ መምህሩ “አሄሄ፣ ብላችሁ ብላችሁ ይቺን ጦጣ ካለ ጅራት ልታስቀሯት ነው መሰለኝ!” አላቸው፡፡]
  8. የሰሞኑን አያድርገውና ከመነሻው ጀምሮ በ11 ቁጥር ፍቅር የተለከፈው ፀሐዩ መንግሥታችን ኢትዮጵያ በዓመት ከ11 በመቶ በላይ ዕድገት እያስመዘገበች ነው ሲል ነጭ ውሸት ከተባለ ድሃዋ ኤርትራ ሠራዊታችንን በባለ አራትና አምስት ኮከብ ሆቴል ውስጥ በልዩ ክብካቤ የያዘልን ያህል ይቆጠራል ቢባል ምን ዓይነት የውሸት ወይም የግነት ስያሜ ሊሰጠው ይሆን? እውነት ትመራለች ብያለሁ፡፡ በጋራ እንኮምኩማትና ይምረረን፡፡ እናስ? የአንድ ሠራዊት ቁጥር ስንት ነው? ይህ በምሥጢር ሊያዝ የሚገባው ጉዳይ ስለሆነ ከማንም መልስ አልጠብቅም፡፡ ነገር ግን 50 ወይም ግፋ ቢል 100 ሰዎችን በባለ አራትም ይባል አምስት ኮከብ ሆቴል መንከባከብ ይቻል እንደሆነ እንጂ አንድን ተዋጊ ሠራዊት ልትፈራርስ የደረሰች ሀገር አንቀባርራ ይዛለች ማለት ለእኔ በቀላሉ የሚዋጥልኝ እውነት አይደለም፡፡ መሆኑን ጠልቼው ሳይሆን የአኳኋኑ ነገር አስገርሞኝ ነው፡፡ ቢሆን ቢሆን ከሠራዊቱ አንደበት ብንሰማው በተሻለ፡፡ ለነገሩ በእግረ መንገድ ትዝ ብሎኝ እንጂ ይህ ችግሬ አይደለም፡፡
  9. አንድ ኅቡዕ ድርጅት የሚሠራቸው ሥራዎች ቢያንስ ለውጤት እስኪበቁ ድረስ ኅቡዕ ናቸው፡፡ “በፖሊስ፣ በጦሩ፣ በደኅንነቱና በመላው የመንግሥት መዋቅር ገብተን እየሠራን ነው፤ ይህንንም ወያኔዎች እንዲያውቁልን እንፈልጋለን…” ማለት ለእኔ በዓለም ታይቶ የማይታወቅ አዲስ የትግል እስትራቴጂ ነው፡፡ እንዲህ አይባልም – በጭራሽ! ለምን? በተጠርጣሪዎች ላይ ልጓሙ እንዲጠብቅና መግቢያ መውጫ እንዲያጡ ነው? እ…? ሕዝብን በደስታ ለማስቦረቅ ወይንስ ጠላትን በሀዘን ከል ለማስለበስ ወይስ ለሁለቱም ዓላማዎች? ይህ ነገር ያልገባኝ፣ ሊገባኝም የማይችል ነው፡፡ የፀጥታና የኢንተሊጀንስ ሥራ እንዲህ በዐዋጅ በሚዲያ እየተነገረ የሚሠራ ከሆነና ውጤታማም የሚሆን ከሆነ በአዲስ ግኝትነቱ እየተደነቅንበት በሌላም በኩል እኛ ኢትዮጵያውያን በዓለም ታሪክ የምናስመዘግበው አዲስ ክስተት ይሆናል፡፡ አይሆንም ብዬ አልከራከርም፤ ምክንያቱም ዓለማችን የብዙ ድንቃ ድንቅ ታሪኮች መፍለቂያ መድረክ ስለሆነች የዚህን ደፋር ዐዋጅ ውጤት ወደፊት ልናይ እንችል ይሆናል፡፡ ስላስገረመኝ አሁን አነሳሁት እንጂ ይህም እንደችግር ሊጠቀስ የሚችል አይደለም፡፡
  10. በሌላት ባጀት ኤርትራ ከኢትዮጵያ ምን ልታገኝ ነው ይህን የመሰለ የቼጉቬራንና የሆ ቺ ሚንን ዓይነት ሚና በአፍሪካ ቀንድ ልትጫወት ቆርጣ የተነሣችው የሚለው ጥያቄ እኔን ብዙም አያሳስበኝም፡፡ á‹« ዛር ወርዶ ተንቀጥቅጦ የሚሆን ነው፡፡ እኔ የምለው ኤርትራ ለዚህ ታላቅ ዓላማ ጅማሮና ስኬት ምንም ዓይነት የሞራል ብቃት የላትም ነው፡፡ ይህን የተቀደሰ ዓላማ ዕውን ለማድረግ ከማሰቧ በፊት ንስሃ መግባት አለባት፤ የካርማ ጽዳት ዘመቻ ማካሄድ አለባት፤ አንድ ሰው በአንድ ጊዜ ሰይጣንና መልዓክ ሊሆን አይቻለውምና የኤርትራ መንግሥት ለዚህ ታላቅ የነጻነት ጉዞ አጋፋሪነት የሚያሳጨው በአሁኑ ሁኔታ አንድም ነገር የለም፤ የምናውቅለት አጠቃላይ ቀውስ ይቅርና ኤርትራ ከዓለም በሀብት አንደኛም ብትሆን የተጨቆነን ሕዝብ ነጻ ለማውጣት በምንም ዓይነት መለኪያ ለምርጫ አትቀርብም፤ የነጻነት ትግል ቀልድ አይደለም፤ የነጻነት ትግል በልምምጥና  እንደቤት ተከራይ የአከራይን እስትንፋስ ጠብቆ የሚካሄድ ትግልም አይደለም፤ መወሻሸት ይቅር፡፡ እናም ኤርትራ ኢትዮጵያን ነጻ ለማውጣት ፍላጎት ከማሳየቷ በፊት ቀድመው መታየት የነበረባቸው ብዙ ቅድመ ሁኔታዎች ነበሩ – ሌላው ሁሉ ይቅር ከወያኔም ጋር ባይሆን ከኢትዮጵያ ሕዝብ ጋር ዕርቅ ለመፍጠር ጅማሮውን በተግባር ማሳየት ነበረባት -  ለምሳሌ እሥረኞችን በመፍታት፣ የበቀደሙን ከናይጄሪያ ጋር ያደረግነውን የእግር ኳስ ጨዋታችንን በቲቪ የስፖርት ዘገባዋ መጥቀስ ወዘተ. (ተከታትያለሁ ያን ታላቅ ኹነት ሳይዘግቡ ዘለሉት – ገረመኝ፤ ኤሪቲቪ ለኛ ያላቸው ፍቅርም በደንብ ገባኝ)፡፡ እኛ ከሦስት ሺህ ዓመታት በላይ ዕድሜ ያላት የታሪክ አምባ የምንላት ሀገራችንን ትናንትና ቅኝ ገዢዎች የጠፈጠፏት የ65 ዓመት ዕድሜ ሀገር ናት የሚሉን አቶ ኢሳይያስ የኢትዮጵያን ነጻነት ከልብ የሚደግፉበት አንድም አሣማኝ ሎጂክ የለም፡፡ “የራሷ አሮባት የሰው ታማስላለች” እንዲሉ ነው ነገሩ፡፡ ቀድሞ ነገር ማን ገሃነም ውስጥ ጨመረንና? ለነገሩ ዕድሜ ይስጠን እንጂ ወደፊት ‹ኢትዮጵያ የምትባል ሀገር ከነአካቴው የለችም› ሊሉንም ይችሉ ይሆናል፡፡

 

በቀጠሮ ወዳቆየሁት ሃሳብ ላዝግም፡፡ ከዚያ በፊት ግን አንድ ነገር ልበል፡፡ ልተወው ብዬ ነበር ግን ግዴለም አንስቼው ልለፍ፡፡ ሰሞኑን በላክሁት ግልጽ አስተያየት ምክንያት ሌሎች ሰዎች ሲወራረፉ፣ ሲወቃቀሱና ይቅር ሲባባሉ በዚህ መከረኛ ኢንተርኔት መወሳሰብ ምክንያት ታዝቤያለሁ፡፡ መጣላታቸውም፣ መወቃቀሳቸውም፣ መታረቃቸውም ጥሩ ነው፡፡ እንደኔ ግን ሁሉም ነገር ከንቱ ነው፡፡ ከዚሁ በተያያዘ በጣም የማከብረውና የምወደው አንድ ግለሰብ በጣም ተበሳጭቶብኝ እንዳልሸጥ እንዳልለወጥ አድርጎ በስድብ ሞልጮኛል፡፡ የተናገርኩት ነገር ሀሰት እውነትነት ሳይሆን ማንነቴ አሳስቦታል፤ የያዝኩት ሃሳብ ክብደትና ቅለት ሳይሆን የት እንደምኖርና በምን ሥልጣን “መካሪ” ሆኜ እንደተገኘሁ አስጨንቆታል፡፡ እኔ ደግሞ ባለፈው ሣምንትም ሆነ አሁን ለምለው ነገር ሁሉ ኢትዮጵያዊነቴ ብቻ በቂ ነው እላለሁ – እንዲያውም በምለው ነገር ትክክለኝነት እስካመንኩ ድረስ ሰው መሆኔ ብቻም በቂየ ነው፡፡ እኔ የምለውን ለማለት በግድ በዶክተራል ዲግሪዎች የተንቆጠቆጠ ሲቪና በግልጽ መድረክ አንቱ የተባለ ስብዕና ሊኖረኝ አይገባም – ይህኛውም ከንቱ ነው፡፡ ቁም ነገርን መምከር የእመክራለሁ ባይ ጣጣ ሲሆን በግትርነትና በዕብሪት ጎዳና በመጓዝ የሚሠነዘርን ሂስና ቀና አስተያየት አለመቀበል የተመካሪ ዕዳ ነው፡፡ እንኳንስ ሰውን ያህል ነገር ሰማይንና ምድርን የመሳሰሉ ግዑዛን ነገሮችም በምልክት ይመክራሉ፤ የተማረ ኃይል ደግሞ ከቃላት ኅብረት ይቅርና ከዱላም ይማራል – ይህም ሊሆን የሚችለው ዕውቀት በቃኝ ብሎ የማወቂያ በርና መስኮቶቹን ጥርቅም አድርጎ ካልዘጋ ነው፡፡ ለአብነት አንድ ሰው ሰማይ ሲጠቋቁር ጥግ ካልያዘ በዝናብ ሊበሰብስ ይችላል፡፡ እንግዲያውስ ሰውማ እንዴቱን ያህል አይመክር?  ይሄ “አንተ ማን ነህ እንዲህ ለማለት? አንተ ምን ቤት ነህ?” የሚሉት ፈሊጥ ደግሞ ጡረታ ሊወጣ ይገባዋል፤ ሊኖር የግድ ከሆነም በጓደኛሞች መካከል የግል ጨዋታ እንጂ የኔንም የወደፊት ዕጣ በሚወስን የጋራ የሀገር ጉዳይ አይደለም፡፡  በዚያ ላይ በድምጽ ብልጫ የሕዝብን  ውክልና አግኝተው የመንግሥትን ሥልጣን በማይዙባትና ማንም በፈለገ ሰዓት ከጫካ ወደቤተ መንግሥት ገስግሶ ሕዝብ ጫንቃ ላይ ፊጥ በማለት ቅንቅኑን በሚያራግፍባት ሀገር ውስጥ ለአንድ ሰው ሃሳብን በብዕር መግለፅ ሲባል ልዩ ዐዋጅ ሊታወጅ እንደማይጠበቅ ወይም ከተቃዋሚ ኃይሎች ሃሳብን በነጻነት የመግለጽ ሊቼንሳ ሊጠይቅ እንደማይገባው መረዳት ይገባል፡፡ እናም እባካችሁን “Who the hell are you to advise ‘this’ or ‘that’” የምትሉኝ ለወደፊቱ አትበሉኝ፡፡ በመሠረቱ በስድብ መጠዛጠዝ ቀላል ነው፤ ብዙ ወጪም የለውም፤ “ደንቆሮ” የሚልህን “ዕውር” ብትለው መሣ ለመሣ ናችሁ፡፡ ነገር ግን የዕድገት ምልክት አይደለም፤ መሰዳደብ ሰውን ያሳንሳል፡፡ አላስችለን እያለ እንጂ እንደውነቱ ከሆነ ስንናደድ ባንጽፍና ባንናገር የተገባ ነበር፡፡ ምክንያቱም ንዴትና ብስጭት በሁለት እብለቶች መሃል የምትሰቃይን እውነት ይበልጥ መቅኖ ያሳጣታል፡፡ እናም ታዲያ ሰይጣን ምን ሠርቶ ይብላ ብዙዎቻችንን እልህና ንዴት ውስጥ እየከተተ ዐይናችንንና ልቦናችንንም በበርኖሱ እየጋረደ ነጩን ጥቁር፣ ጥቁሩን ነጭ ያደርግና የአንዲት እናት ልጆችን በከንቱ ያባላናል፤ ይህም ለጊዜው ነው፡፡

እውነቱን እንነጋገር ካልን የሀገር ጉዳይ የአምባቸውና የሐጎስ ወይም የጫልቱና የአብረኸት ጉዳይ ብቻ አይደለም፡፡ የአንድ ግለሰብ ፖለቲካዊም ሆነ ሃይማኖታዊ ተፅዕኖ ቀላል ባይሆንም በሀገር ጉዳይ ግርማና በቀለ የብድር ጦርነት ፈጥረው በብዕር ቢተጋተጉ ጅሎች ናቸው፡፡ ሰው በግል ከአንድ ሌላ ግለሰብ ጋር የሚጣላው በድንበር ይገናኝና፣ በመጠጥ ቤት ውስጥ በነገር ቁርሾ ወይም በሴትና በመሳሰለው ይቆራቆስና፣ በአንድ መሥሪያ ቤት ውስጥ በ“ታዘዝ” “አልታዘዝም” ቅራኔና አለመግባባት ይፈጠርና … ሰዎች እስከ ሕይወት ኅልፈት ሊጋጩ ይችላሉ፡፡ ነገር ግን አንድ ሰው ስለሀገሩ የመሰለውን በመናገሩ ብቻ ያለ የሌለ ስድብና ዛቻ ቢራገፍበት አግባብ አይመስለኝም – በዚያም ላይ “እዚያም ቤት እሳት አለ” የሚለውን የአለቃ ገ/ሃና ተረት ማስታወስም ይገባል፤ ምክንያቱም “የሚሰድቧችሁን መርቁ” የሚለው ወርቃማ ምክረ – ቃል በማኅበረሰባችን ውስጥ ገና በቅጡ አልሰረፀምና፡፡ ደግሞም “ሕጻኑን ከነታጠበበት ውሃ መድፋት” መልካም ነገር አይደለም፡፡ አንድ ሰው ጥፋት ቢያጠፋ በጥፋቱ ብቻ ይጠየቅ እንጂ ወደሰብኣዊ ማንነቱ እየገባንና ያለፈ ታሪኩን እያስታወስን በነገር መንሽ ልናበራየው አይገባም፡፡ እንዲህ የምለው ስለሌሎችም እንጂ ስለራሴ ብቻ አይደለም፡፡ እስኪያልፍ ማልፋቱ ከፋ እንጂ በመሠረቱ ይህ ዓይነቱ የደካማ አስተሳሰብ ውጤትም ዑደቱን ጠብቆ ማለፉ የማይቀር ነው፡፡ ለጊዜው ግን ክፉኛ እየጎዳን መሆኑ ይሠመርበት፡፡

በሀገራችን ብዙ ችግሮች አሉ፡፡ በሥልጣን ላይ ያሉትም ሆኑ በተቃውሞው ጎራ የተሠለፉት የሚጋሯቸው በርካታ ባህርያት እንዳሏቸው ከግምት ባለፈ አስረግጦ መናገር ይቻላል፡፡ ከሞላ ጎደል የሁሉም ጎራዎች ባለሥልጣናት የዴሞክራሲ ጽንሰ ሃሳብ በተግባር ብቻ ሣይሆን በስም እንኳን በቅጡ ይጠራበት ባልነበረበት የፊውዳል  ሥርዓት የተወለዱ ናቸው ቢባል ብዙ አልተጋነነም፡፡ ባህላችንም – በተለይ የቅርብ ጊዜው – የእልህና የ“እኔ ካላሸነፍኩ ሞቼ እገኛለሁ” ዓይነት የ“ቆይ ብቻ!” መፈክር ልክፍት የተጠናወተው ነው፡፡ አስተዳደጋችን፣ ሃይማኖታችን፣ ማኅበረሰባችን … ቀርፀው ያሳደጉን አሁን የምናስተውላቸውን አጠቃላይ ፖለቲካዊና ማኅበራዊ ችግሮች ለመጠንሰስና ፋፍተው እንዲያምሱን ለማድረግ ካልሆነ በስተቀር ችግሮቻችንን ሊቀርፍ በሚችል ሁኔታ የገነቡን አይመስልም፡፡ በመሠረቱ የኢትዮጵያውያን ሆኑ የሌሎች ሀገሮች ፖለቲከኞች ዘመን የማይሽረው ፋሽን እነዚህን የፈረደባቸውን “ዴምክራሲ፣ሰላም፣ ነጻነት፣ ፍትህ፣ ወንድማማችነት፣ እኩልነትና ነጻነት” የሚባሉትን አእሩግ ቃላተ-መጽሐፍ በመጠቀም ሕዝብን ማነሁለል ነው፡፡ እነዚህን ቃላት የማይጠቀም የለም፡፡ እነሂትለርና ሙሶሊኒም ሳይጠቀሙባቸው አይቀሩም ብዬ አስባለሁ፡፡ በተግባር ግን ሁሉም ሀገሮቻቸውንና ሕዝቦቻቸውን ከእሥረኛነት ባልተናነሰ አንዳንዴም በበለጠ ያሰቃዩና የሚያሰቃዩም ናቸው፡፡ የኛዎቹ የሚለዩት ደግሞ ባህላችን ያዳበረላቸውን የእኔነት ጠባይ ኢምፖርት ባደረጉት የማጭበርበሪያዋ የዴሞክራሲ ካባ እየጀቦኑ ሕዝብ መፈጠሩን እስኪራገም በየተራ የሚያንገላቱና የሚያንገበግቡ መሆናቸው ነው፡፡ አሁንም ይህም ያልፋል  የሚል ፅኑ እምነት አለኝ፡፡

በአንዳንድ አባቶች አስተምህሮ መሠረት ኢትዮጵያና ኤርትራ አንድ ይሆናሉ፡፡ ያም ጊዜ በከፍተኛ ፍጥነት እየመጣ ነው፡፡ የተለያዩት በግፍ ነው፡፡ የግፍ ጊዜ ደግሞ እንደማንኛውም ሌላ ነገር ሁሉ መጀመሪያ እንዳለው መጨረሻም አለው፡፡ á‹« መጨረሻ ነው እንግዲህ እየመጣ እንደሆነ በመነገር ላይ የሚገኘው፡፡ አንድ የሚሆኑትም ለዬብቻቸው የቀመሱት የመከራ ገፈት ተመሳሳይ እንደመሆኑ የቀደመው የአብሮነት ዘመን እንደሚሻላቸው በመሪር የሕይወት ተሞክሮ ስላረጋገጡ ነው፡፡ ስለሆነም የጎጃም ጤፍና ማር፣ የወለጋ ቅቤና ወርቅ፣ የሲዳሞ አትክልትና ፍራፍሬ፣ የከፋ ቡናና ጣውላ፣ የሸዋ ክትፎና ቆጮ… ማይጨውና መቀሌን አቋርጠው ወደ አሥመራ በስካኒያና በቱርቦ የሚሄዱበት፣ ከአሥመራም የፋብሪካ ውጤቶች ወደ መሀል ሀገር የሚጓጓዙበት ዘመን ይመጣል (መሎቲን ለማጣጣም ምን ያህል እንደናፈቅሁ አትጠይቁኝ!)፡፡ “አገባሻለሁ ያለ ላያገባሽ፣ ከባልሽ ሆድ አትባባሽ” የሚለውን ነባር ብሂል በቅጡ የተረዳው የኤርትራ ሕዝብ ባሳለፈው የ22+ ዓመታት የስቃይ ኑሮ ብዙ ተማሯል፤ ተምሯልም፡፡ ቀሪው የኢትዮጵያ ሕዝብም በወያኔና በሻዕቢያ ጣምራ አገዛዝ በደረሰበት መጨረሻ የሌለው ግፍና በደል ብዙ ተንገፍግፏል፤ የለያዩትን ሽብልቆችና የፍቅር መቀሶችንም ጠንቅቆ ስለሚያውቅ የኤርትራ እህትና ወንድሞቹን በእቅፉ ለመቀበል ተዘጋጅቷል – ወዳጅ ዘመድ የሚደሰትበት ጠላት አንጀቱ የሚያርርበት ዘመን እየገሰገሰ ነውና ደስ ይበለን፡፡ ሰዎች እንዳመለካከታቸው ብዙ ሊናገሩ ቢችሉም በሁለቱም ሕዝቦች ሆድ ውስጥ ግን በ“ለምን ተለያየን” ብዙ ቁጭትና ጸጸት መኖሩ ግልጽ ነው፡፡ በሁለቱ ሕዝቦች ዘንድ የተፈጠረ የሚመስለው ችግር ሰው ሠራሽ እንጂ ተፈጥሯዊ እንዳልሆነ ያስታውቃል፤ ጤነኛ የሆኑ የሁለቱም … ዜጎች ያውቃሉ (“ሀገራት” ማለቱ ሁልጊዜ ይቀፍፈኛል”፡፡ በድብቅ አንዳንዴ ደግሞ በግልጽ እንደምናየው አንዳቸው ለአንዳቸው ያላቸውን ናፍቆት ይገልጣሉ፡፡ የኤርትራንና የቀሪዋን ኢትዮጵያ ቴሌቪዥኖች ባየህበት ዐይን የኬንያንና የሱዳንን ወይም የጂቡቲንና የጓቴማላን ቲቪዎች ተመልከት – ሰማይና ምድር ናቸው፡፡ የኛና የኛ ግን ቋንቋው፣ ባህሉ፣ ሃይማኖቱ፣ አለባበሱ፣ ዘፈኑና አዘፋፈኑ፣ አለባበሱ፣ ምግቡና አመጋገቡ፣ ጭውውቱና ትያትሩ፣ አጻጻፉና ሆሄው፣ ጭፈራና ሳስኢቱ(እስክስታው)፣ .. ከሞላ ጎደል አንድ ነው – እግዜር አንድ አድርጎ የፈጠረውን ማን ሊለየው ይችላል ታዲያ? ወጀቡን ተውት፤ የግማሽና ሩብ ምዕተ ዓመቷን የኮምፓስ መሠወር ብዙም ከጉዳይ አትጣፉት፡፡ ዕድል ሲጣመም አንዳንዴ ሊያጋጥም እንደሚችል እንግዳ ክስተት እንቁጠረውና ለመጪው ታሪካዊ ኹነት እንሰናዳ ይልቁንስ፡፡ ኤሪቲቪን የሚመለከት ኢትዮጵያዊ የሁለቱን ምስስሎች በንጹሕ ኅሊናው ካጤነ “እንኳንስ የሄዱ!” በሚል የበቀለኝነት ስሜት ሳይሆን “ለምን ሄዱብኝ” በሚል የቁጭት ስሜት ነው መላ ሰውነቱ የሚረበሽ፡፡ ለነገሩ መጋጨት ያለ ነው – በኛም አልተጀመረም፡፡ እንኳንስ ሻዕቢያንና ወያኔን የመሰሉ የለዬላቸው ጭራቆች ተፈጥረውብን በተራ ነገርም ቢሆን መጣላት ይኖራል፡፡ ነገር ግን ሁሉም ጠብ ግዘፍ ነስቶ አሁን በመካከላችን የተከሰተውን የመሰለ ሰፊ ክፍተት መቼም ቢሆን ሊፈጥር አይገባም – በትልቅ ዋጋ ትልቅ ትምህርት ተምረናል፡፡ ሀገር ሲያረጅ ጃርት እንደሚያፈራ ኢትዮጵያም አርጅታ ኢሳይያስንና መለስን የመሰሉ ጉዶች ተፈጠሩና ደጋፊና ረዳትም ከውጪና ከውስጥ አገኙና ይህችን ማለፊያ ሀገር ለጊዜውም ቢሆን እንዳትሆን አደረጓት፡፡ ቢሆንም ሁሉም ነገር ለበጎ ነውና ለመጪው ጊዜ ማማር እንዲህ እናድርግ፡፡

ቃሉ አይታጠፍም፡፡ የእግዚአብሔር ቃል አለ፡፡ ያም ቃል ሁላችንም ለተወሰነ ጊዜ መሰቃየታችን የማይቀር መሆኑ ነው፡፡ ስቃዩም አለፈ – እያለፈም ነው፡፡ ከአሁን በኋላ ማድረግ ያለብን መጀመሪያ ከራሳችን ጋር መታረቅ ነው፡፡ ከራሳችን ጋር መታረቅ ሲባል ለምሳሌ እኔ ከራሴው ጋር መታረቅ እንደማለት ነው፡፡ ከራሱ ጋር ያልታረቀ ሰው ከሌላ ሰው ጋር ሊታረቅ አይቻለውም፡፡ ከራስ ጋር መታረቅ እንዴት ይቻላል? ቀላልም ከባድም ነው፡፡ ግን ካሰብንበት እንችላለን፡፡ በበኩሌ እየሞከርኩ ነው፡፡ እንደእግዚአብሔር ፈቃድ ይሳካልኝ ይሆናል፡፡

ሰው በተፈጥሮው ሁለት ነው፡፡ አንድም ሥጋ አንድም ነፍስ፡፡ ይህን ማንም ያውቃል፡፡ ሦስተኛም መንፈስ አለ፡፡ ይህ መንፈስ አንድም ደግ ነው አንድም ክፉ ነው፡፡ የመገኘታቸው ምጣኔ በሚለያይ መልኩ በአንድ ሰው ውስጥ የሚመሽጉ ሁለት ተቃራኒ መንፈሶች አሉ ማለት ነው፡፡ አንዲት ሴት ጓደኛዋን “ነገ እሁድ ቤተ ክርስቲያን እንድንሄድ በጧት እቀሰቅስሻለሁ” ስትላት “ወንዶቹ እንዳሳደሩን” እንዳለችው እኛም ውለን እምንገባው በነዚህ መንታ መናፍስት ግፊትና ምሥጢራዊ ተፅዕኖ ነው፡፡ በዚያ ላይ የሕይወት መጽሐፍን እናስብ – ሁለ ነገራችን በየዕለቱ በመልክ በመልክ የሚመዘገብበት ነው፡፡ ደግ ሥራ በደግ መዝገብ፣ ክፉው ሥራ በክፉው መዝገብ፡፡ እዚህ ላይ “karma” (ከራማ?) የሚለውን የባዕድ ቃል እናስታውስ፡፡ ይህን ካርማ የምንለውን በሕይወት መጽሐፍ እንተካና ፍልስፍናችንን ወደፊት ጥቂት ገፋ እናድርገው፡፡

የጸዳ ካርማ ያለው ሰው ቆሻሻ ካርማ ካለው ሰው ይለያል፡፡ ወደዚህ ዓለም የመምጣታችን ምሥጢር እንግዲህ እዚህ ላይ ነው ግዘፍ የሚነሳው፡፡ አመጣጣችን ለመማር ነው፤ ተምረንም ለማደግ፡፡ በዓለማዊ አስተሳሰብ ለዓለማውያን ትምህርት አያልቅም፡፡ በመንፈሳዊ አስተሳሰብ ግን ለመንፈሣውያን ትምህርት እንደሚያልቅ ይነገራል፡፡ የዚህን ዓለም ትምህርት ተምሮ የሚጨርስ ብፁዕ ሆነ እንደማለት ነውና በሌላ እንጂ በዚህኛው ዓለም ቦታ የለውም ይባላል፡፡ ይህ ዓለም የመማሪያ ቦታ ነው ከተባለ ዘንዳ ለምሳሌ አምና ውሸታም የነበረ ሰው፣ ታችአምና ተሳዳቢ የነበረ ሰው፣ የዛሬ አምስት ዓመት ሌባ የነበረ ሰው፣ ከዚያ በፊት አመንዝራ የነበረ ሰው … አሁንም እንደዚያው ከሆነ ሰነፍ ተማሪ መባሉ ነው፡፡ ጎበዝ ተማሪ ማለት በአንድ ሕይወት ብቻም ሣይሆን በአንድ አጋጣሚም ብዙ ነገር ተምሮ የሚያልፍ ነው፡፡ ሰነፍ ተማሪ ግን በአንድ ቀርቶ በዘጠኝም አይማርም፤ “ዕወቅ ያለው በዐርባ ቀኑ ያውቃል፤ አትወቅ ያለው ግን በዐርባ ዓመቱም አያውቅ” አይደል የሚባል? በዚህች ምድር ትምህርት የምንለው ካርማን ማጽዳት ነው ወንድሞችና እህቶች፡፡ ነፍስን የሚያቆሽሽ ነገር ሁሉ ይበልጡን ለሥጋ ምቾት የተፈጠረ ነው፡፡ ንፉግነትን፣ ስግብግብነትን፣ ዘረኝነትን፣ወዘተ … የምታራምድ ሥጋ የካርማ መቆሸሽ ገጥሟታልና ደባሏን ነፍስ ታሰቃያታለች፡፡ የካርማ መቆሸሽ ደግሞ አፈር ላይ የወደቀ ሥጋ እንደማለት ነው – ከአንዱ ወደ ሌላው በቀላሉ ይጋባል፡፡ ፍቅርን፣ ሰብኣዊነትን፣ ርህራሄን፣ … የመሳሰሉ የዩኒቨርሳሊቲ መገለጫዎችን የሚያራምድ የነፍስና የሥጋ ጥምረት ግን ባለቤቱን በካርማ ንጽሕና ታስከብራለች፤ ከተደጋጋሚ የመንፈስ ድቀትም ታድነዋለች፡፡ የመንፈስና የሥጋ ሀብት በዓይነትም በመለኪያም ይለያያሉ፡፡ …

ፍቅር ታጋሽ ነው፤ ፍቅር ስለፍቅር ሟች ነው፡፡ በፍቅር ውስጥ ስግብግብነት የለም፤ ለእናንተ ወይ ለአንተ እንጂ ለኔ ወይ ለኛ ብቻ ብሎ ነገር በእውነተኛ ፍቅር ዘንድ ቦታ የለውም፡፡ ለዚህም ነው የፍቅር ተምሳሌቱ ኢየሱስ ክርስቶስ ለዓለም ሲል በመስቀል ተቸንክሮ የሞተው፡፡ በክርስቶስ ስም የተመዘገበ በቢሊዮን የሚቆጠር ገንዘብ ቀርቶ ማረፊያ የምትሆነው የወፍ ጎጆ እምታህል መኖሪያ ቤት እንኳን በራሱ ስምም ሆነ በቤተሰቡ አስመዝግቦ አላለፈም – ዘመናችንን ግን ተመልከቱ፤ ለሰባና ሰማንያ ዓመት ዕድሜ 60 እና 70 ቢሊዮን ዶላር አላግባብ በሆነ መንገድ የሚያጠራቅሙ ገንዘብን አምላኪዎች አሉ፡፡ ይህን ገንዘብ ለመሥራት ስንቶች የዓለም ምዝብር ሕዝቦች አጥንታቸው እንደሚጋጥና መቅኒያቸው እንደሚመጠጥ አስቡት፤ ይህ ነው የኔጌቲቭ ካርማ አንዱ የዘወትር ቀለብ፡፡

በፍቅር ግን እንዲህ ያለ መስገብገብና ለፍቅረ ንዋይ መንበርከክ የለም፡፡ ፍቅር ስለሌሎች እንጂ ስለራስ ብዙም አይጨነቅም፡፡ የፍቅርን ጦር ያነገበ ሞቶም እንኳን ያሸንፋል እንጂ ሽንፈት አያውቀውም፡፡ በፍቅር ውስጥ ቂም በቀል የለም፡፡ በፍቅር ውስጥ በ“እንዲህ አድርገኸኝ!” ቁዘማ የእልህ መወጣጫ ጊዜ በጉጉት አይጠበቅም፤ ፍቅር ጠብንና ግጭትን የሚደመስስ መግነጢሳዊ ኃያል አለው፡፡ በፍቅር ውስጥ ስትመላለስ የበደለህን እንደበዳይ ሆነህ እስከመካስ የምትሄድበት ሆደሰፊነት አለ፡፡ የቆሸሸ ካርማ ግን የአለመርካትና የአለመጥገብ ጥቁር ዋሻ ነው፡፡ እየበሉ መራብ፣ እየጠጡ መጠማት፣ እያገኙ ማጣት… ያለው በቆሸሸ ካርማ ውስጥ ሲኖሩ ነው፡፡ ሳይበሉ መጥገብ፣ ሳይጠጡ መርካት፣ እያጡ ማግኘት… ያለው ደግሞ በፍቅር ውስጥ፣ በንጹሕ ካርማ ዘንድ ነው፡፡ ካርማችንን እንጠብ! (karma cleansing ይሉታል ባለሙያዎቹ – ይህንንም ሙያ ካልነው፡፡) ያኔ ከየታሠርንበት ጎረኖ ወጥተን አይደለም የበሬ ግምባር ከምታህል ኢትዮ-ኤርትራ መሬት ልንገነጣጠል አፍሪካውያን ሁሉ ተስማምተን መላዋን አፍሪካንም በአንድ ሉዓላዊ መንግሥት ሥር እናውላለን፡፡ የሥልጣን ሱስ፣ የሀብት አራራ፣ የአድልዖ á‹°á‹Œ … የሚጠናወተን በፍቅር ስንኖር ሳይሆን በኔጌቲቭ ካርማ ውስጥ ከዕኩይ መንፈስ ጋር ስንወዳጅ ብቻ ነው፡፡

ኢትዮጵያችን በቆሸሸ ካርማ የአገዛዝ ቀምበር ሥር ነበረች፤ አሁንም እንደዚያው ነች፡፡ ከህዝቧም ብዙዎቻችን የቆሸሸ ካርማ ተጠቂዎች መሆናችንን ማኅበረሰብኣዊ ሕይወታችን ያሳብቅብናል፤ የነፍስ ጣርና መዋተት በብዛት እንደሚስተዋል ኑሯችን አፍ አውጥቶ ይናገራል፡፡ ከዚህ አዘቅት ለመውጣት በመላዋ ኤርኢትዮጵያ ውስጥ የሚገኙ ዜጎች ወደፍቅር አምባ መምጣት አለባቸው፡፡ ፍቅር አይግደረደርም፡፡ ፍቅር አይፈራም፤ አያፍርምም፡፡ ፍቅር ሀሰትንና ያልተገባ ይሉኝታን አያውቅም፡፡ ፍቅር እውነት ነው፡፡ እውነትም እግዚአብሔር፡፡ እግዚአብሔርን ማንም በሚያውቀውና በሚገባው ቋንቋ ቢጠራው ችግር የለውም፡፡ በእግዚአብሔር ቤት፣ በፍቅር ቤት፣ በእውነት ቤት ደግሞ መከፋፈል ብሎ ነገር የለም፤ መጣላትና መሰዳደብ የለም፤ መተማማትና መዘራጠጥ የለም፡፡ መከፋፈልና ጥልና አምባጓሮ በመደበኛነት ተንሠራፍቶ የሚገኘው በጨለማው የክፉ መንፈስ ግዛት ውስጥ ነው፡፡

የኢትዮጵያ አንድነት እውን ሊሆን የሚችልባቸው ሁለት መንገዶች ይታዩኛል፡፡ አንዱ በጣም ተስፋ ያስቆርጠኛል፡፡ ሌላው ግን የማይቀር ነው፡፡ ተስፋ ያስቆርጠኛል የምላችሁ በኢሳይያስ አፈወርቂና በመለስ በኩል እጠብቀው የነበረው ነው፡፡ ነገር ግን እስከቅርብ ጊዜ ድረስ አንጋጥጬ ብጠብቅም በተለይ አቶ ኢሳይያስ አምላክ ለንስሃ የሰጣቸውን ረጂም ጊዜ ሊጠቀሙበት አልቻሉም – የካርማቸው መጨለም ግን እያንገላታቸው እንደሆነ በተዛዋሪም ቢሆን እሰማለሁ፡፡ ስለዚህ ከእርሳቸው በኋላ ሌላ ዕድለኛ አለ ማለት ነው – በቡድንም ሊሆን ይችላል፡፡ አቶ መለስም ይህ ዕድል ነበረው፡፡ ግን ሳይጠቀምበትና ምናልባትም ንስሃ ሳይገባ የሞተ ይመስለኛል፡፡ ምሕረትን ማግኘት አለማግኘቱ የፈጣሪ ድርሻ ቢሆንም አንዲት ታላቅ ሀገር አፈራርሶ ለአምባገነኖች ገና ለጋ ነው በሚባል ዕድሜው ፈራርሶ መሞት ያጸድቃል የሚል እምነት የለኝም፡፡ ትልቁ ነገር ያሉት ካለፉት አንዳች ነገር መማር እንዲችሉ የፍቅር አምላክ የሆነው የሠራዊት ጌታ እግዚአብሄር ቢረዳቸው መልካም በሆነ ነበር፡፡ የማንም መኮነን ማንንም አይጠቅምም፡፡ ለማንኛውም ፈጣሪ ይርዳንና የነጻነቲቱን ቀን በቶሎ ያሳየን፡፡

በመጨረሻየ መጨረሻም ለምን ይህን ጽሑፍ ጻፍኩ? ልበልና ራሴኑ ልጠይቅ፡፡ ከፈለግን ከዚህ ጽሑፍ ብዙ ነገር መገንዘብ እንችላለን ብዬ አስባለሁ፡፡ እኔ ራሴ የተማርኩት አንድ ትልቅ ነገር አንድ ሰው እንዳይጽፍ ወይ እንዳይናር አስበን በስሜት-ወለድ ቅስምን ሰባሪ ቃላት ብንወርፈው ልናቆመው የማንችል መሆናችንንና በዚያ ምትክ ይልቁን በፍቅርና በአዘኔታ ብናቀርበው ወዳጃችን ሊሆን እንደሚችል፣ በርግጎም እንደድርጭት ከመካከላችን ቱር ብሎ እንዳይወጣ የሚያግዘው መሆኑን ነው፡፡ ሌሎች ልባም አንባቢያንም እንደዬምልከታ አቅጣጫቸው የተለያዬ ነገር እንደሚያስታውሱበት አምናለሁ፡፡ እኔ አሁን ስለግለሰቦች ያለፈ ታሪክ፣ ስለግለሰባዊ የባሕርይ ትንተና፣ ስለነጻነት አላስፈላጊነት … አልጻፍኩም፡፡ በበኩሌ ቢሣካልንና ብንለምደው ትናንትን በበጎነቱ ለዛሬ የሚጠቅም አንዳች ነገር ካላገኘንበትና ለዛሬ አዙረን ካልተጠቀምንበት በስተቀር “እንዲህ አልነበርክም? አናውቅህምና ነው? …” እየተባባሉ መተነኳኮሱ የተሸናፊነት ስሜት መገለጫ ይመስለኛል፡፡ ለውጥ የግለሰብም ይሁን የማኅበረሰብ ማዕከላዊ የዕድገት መሠረት መሆኑን ከሚረዳ ሰው ዱሮ ባለፈ የሰዎች ወይም የድርጅቶች ታሪክ መወዛገብ ያለበት አይመስለኝም፡፡ ማተኮር ተግባሩ ላይ ነው – አሁን ላይ እሚፈለገው ተግባር ላይ፡፡ ባልና ሚስት ይመስል ባለፈ ነገር መነዛነዙ ወደፊት የማያራምድ ሽምቃቅ ነው፡፡ ስለዚህ ፈታ እንበል፡፡

በሌላም በኩል ይህን ጽሑፍ ያነበበ አንዳንድ ሰው ድከም ብሎት እኔን በልዩ ልዩ ታርጋዎች ሊያስጌጠኝ ይሞክር ይሆናል፡፡ ይህም ከንቱ ነው፡፡ የጽሑፉን የፊት ለፊት ይዘትና ትርጉም አልፎ ወደ ውስጥ በመግባት በአማሣኝ ነገር መጠመድ ሞኝነት ነው፡፡ የዚህ ድርጅት አባል ነው፤ የዚህኛው ተቃዋሚ ነው፤ አይ ወያኔ ነው፤ የለም ሸንጎ ነው፤ የምን ሸንጎ መድረክ ነው እንጂ፤ አሄሄ… ኧረ የደርግ ርዝራዥ ነው፤ በፍጹም – የኦነግ አባል ነው፤ እንዴት ተደርጎ – ኢሕአፓ ነው እንጂ፤ ኧረ ግዴላችሁም የሰማያዊ ወይም የአረንጓዴ ፓርቲ አባል ሣይሆን አይቀርም፤ ለምን – ኢራፓ ነው እንጂ፤ አሃ፣ ምን ማለትህ ነው የ“አንኮበር ነጻ አውጪ ግምባር” አባል መሆኑን ሰው ነግሮኛል ‘ባክህ  … ትወራውና ፍረጃው ማለቂያ የለውም፤ አንዱ ስለሌላው ማንነት ሲጨነቅ የሚውልበትና የሚያድርበት ከኢትዮጵያ ውጪ ሌላ ሀገር ጥቀሱ ብትባሉ ስለማግኘታችሁ እሰጋለሁ፡፡ አንድ እርምጃ ወደፊት ስንል አምስት ወደኋላ እየጎተተ ከሀገር በታችና ከሥልጣኔ ማማ ሥር የጎለተን፣ በዚያም ምክንያት የቀሪው ዓለም መሣቂያና መሣለቂያ አድርጎ ያስቀረን መቼ እንደተፈጠረብን በውል ያልገባኝ ይህ ዓይነቱ ጠባያችን ይመስለኛል – እርስ በርስ በመጎሻመጥና በመፈራረጅ ወርቃማ ጊዜያችንን እናባክናለን፡፡ ተነግረው የማያልቁ ቀያጅ ችግሮች አሉብን፡፡ እባብ ሲያረጅ ቆዳውን ገፍፎ ይታደሳል አሉ፡፡ አሁንም “ምን አገባህ?” እንዳልባል እንጂ እኛም እንደሀገርም እንደሕዝብም አርጅተናልና እስኪ አንድ መሠረታዊ ለውጥ አምጥተን “ቆዳችን”ን እንግፈፍና እንታደስ፡፡ እግዚአብሔር ሆይ አሁኑኑ ናልን!!!

 

ምርቃት፡- “ስንቱን አጣን” በሚል ርዕስ ፕሮፌሰር መስፍን ወ/ማርያም የጻፉትን አጭር ግን እጅግ መሳጭ መጣጥፍ እንድታነቡ ልጋብዛችሁ፡፡

Happy
Happy
0 %
Sad
Sad
0 %
Excited
Excited
0 %
Sleepy
Sleepy
0 %
Angry
Angry
0 %
Surprise
Surprise
0 %
    Print       Email
  • Published: 11 years ago on October 24, 2013
  • By:
  • Last Modified: October 24, 2013 @ 10:12 am
  • Filed Under: Ethiopia
  • Tagged With:

Average Rating

5 Star
0%
4 Star
0%
3 Star
0%
2 Star
0%
1 Star
0%
<"Without the support of our readers, the Maleda Times website would not exist in its present form">

You might also like...

በሰሜን ሸዋ ዞን ኤፍራታ እና ግድም ወረዳ መከላከያ ከአማራው ማህበረሰብ እና ከፋኖ ጋር ጦርነት ገጥሟል

Read More →

This site is protected by wp-copyrightpro.com

%d bloggers like this:
Skip to toolbar