www.maledatimes.com የመለስ “ተወዳጅነት” ለኢህአዴግ ምኑ ነው!? - MALEDA TIMES
Loading...
You are here:  Home  >  Ethiopia  >  Current Article

የመለስ “ተወዳጅነት” ለኢህአዴግ ምኑ ነው!?

By   /   September 3, 2012  /   2 Comments

    Print       Email
0 0
Read Time:11 Minute, 45 Second

የርዕሷ ዜማ በ

የመለስ “ተወዳጅነት” ለኢህአዴግ ምኑ ነው!?

አንድ ወቅት ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ “የአክሱም ሀውልት ለደቡብ ምኑ ነው!?” ሲሉ የተናገሯትን ትመስላለች። እናም ለዜማ ኩረጃዬ ይቅርታ ጠይቄ እቀጥላለሁ።

አሁን አሁን ኢህአዴግ ምን እየሰራ እንደሆነ እጅግ በጣም ግራ እየገባኝ መጥቷል… “ገና አሁን!” ብለው ሲጠይቁኝ ይታየኛል። እኔም አይ ገና አሁን ሳይሆን አሁንም ድጋሚ በጣም ግራ እየገባኝ ነው!? እልዎታለሁ። የምሬን እኮ ነው…

አቶ መለስ ሞቱ በተባለ ሃያ አራት ሰዓት ባልሞላ ጊዜ ውስጥ አስከሬናቸው አዲሳባ ይገባል ተባለ። በነገራችን ላይ ይሄ ፍጥነት አቶ መለስ የሞቱት ቀድመው ነው። የሚሉትን ወገኖች ንግግር ይበልጥ ያጠናክረዋል። ይሄንን እንተወው እዚህ ግባ የሚባል ወሬ አይደለም። ኢቲቪም ሆነ አቶ በረከት እንደሆኑ “ሰው ያምነናል” ብለው ይናገሩ እንጂ ሁሉም በየጓዳው “አዬ..ዬ…” እንደሚለቸው እናውቃለን…!

(እንኳን ይቺንና የአበል ለቅሶ እንለያለን…!)

የሆነው ሆኖ ለአቶ መለስ በርካታ ሰው አለቀሰላቸው። እንደ እውነቱ ከሆነ ትክክለኛው የአቶ መለስ አዛኞች የመጀመሪያው ቀን እየዬ ብለው ቦሌ አየር መንገድ የታዩት ናቸው። ከዛ በኋላ ይሄንን ያኽል ሰው ይመጣል ብለው ያልጠበቁት እነ ጋሽ ኢህአዴግ ልክ ባለፈው ጊዜ አቶ መለስ የዘጠና ሰባቱን የኢህአዴግ ሰልፍ ሲያዩ አቅላቸውን ስተው “ይሄንን የህዝብ ማዕበል ይዘን ማጭበርበር ሳያስፈልገን ምርጫውን እናሸንፋለን…!” እንዳሉት አይነት “ይሄንን የህዝብ ማዕበል ይዘን በለቅሶ እድገት እመርታ እናሳያለን” ብለው ለራሳቸው ቃል ገቡ። ገቡናም ለሚቀጥሉት አስራ ምናምን ቀናት ህዝቡን ለማስለቀስ ተማማሉ፤

ከዛስ…

ከዚያ ሲያስቡት ያንን ሁሉ ቀን ሰው ከየት ይመጣል? እርግጥ ነው ቤተ መንግስቱ በጎብኚዎች መጨናነቁ አልቀረም ምክንያቱ ደግሞ ቤተመንግስቱን በደህናው ጊዜ ማንም አይቶት ስለማያውቅ በዚህ አጋጣሚ መጎብኘቱ ለብዙዎች ደስታን ስለሚፈጥርላቸው ነው።

በነገራችን ላይ አንድ ወዳጃችን የጠቅላይ ሚኒስትሩን አስከሬን የጫነው መኪና በህዝብ ታጅቦ ሲያይ ምን እንዳለን ነግሬዎታለሁ እንዴ…? ምን አለ መሰልዎ? “አቶ መለስ ዛሬ ገና ህዝቡን ሳይፈሩ አየኋቸው” ብሎናል… እኛም መሞት ደጉ ብለን አደንቀናል!

እዝችው ጋ ያቺን ቀልድ እናምጣት፤ አቶ መለስ ሆዬ በአንዱ ቀን ከአየር ማረፊያ መንገድ አዘግተው እየከነፉ ወደ ቤተመንግስታቸው ሲሄዱ አንዲት ሴትዬ ጭር ባለው መንገድ ላይ ድንገት ተከሰቱ፤ ይሄኔ ፌደራል ፖሊሱ ሴትዮዋን ጋማቸውን ይዞ ወደ ግድግዳ ፊታቸውን አዙሮ ክላሹን ደገነባቸው። ወይዘሮዋ ደነገጡ ሊረሽኑኝ ነው እንዴ…? ብለው በቀስታ ዘወር ሲሉ ፖሊስ ሆዬ፤ “ዙሪ ወደዛ…” ብሎ ፊታቸውን ከግድግዳው ጋር አጣበቀው…!” ልክ አቶ መለስ ካለፉ በኋላ “ከውካዋ አሮጊት… በይ ሂጂ ከዚህ…!” ብሎ ተቆጣቸው። ይሄኔ ሴትየዋ ሃይላቸውን አሰባሰበው “የኔ ጌታ ይቅርታ አድርግልኝና ሰውየውን የምትጠብቋቸው ከቡዳ ነው ከጥይት!?” ብለው ጠየቁ።

አቶ መለስ ዜናዊ በህይወት እያሉ፤ “የልማት አርበኞችን” ሊሸልሙ ካልሆነ በስተቀር ከህዝብ ጋ ተቀላቅለው አይተናቸው አናውቅም። ቤተ መንግስታቸውም ቢሆን ግድግዳውን እንኳ ተጠግቶ መሄድ አይቻልም። ፎቶግራፍ ማንሳትም አይቻልም። አረ ትክ ብሎ ማየት መቻሉንም እንጃ…

ታድያ ልክ አሁን ሲሞቱ እኔ ከሞትኩ እንዳለችው እንስሳ… (ለሞተ ሰው አህያ አይባልም ብዬ ነው!) እርሳቸው ከሞቱማ ተብሎ ያለ ፍተሻ ሁሉ ቤተ መንግስት መገባቱን አይተናል። እስከዛሬ ሲጠበቁ የነበሩት ለካ እርሳቸው እንጂ ቤተ መንግስቱ አልነበረምና…!?

እኔና ሌሎች በርካቶችን የገረመን ነገር አቶ መለስ በህይወት ዘመናቸው ዱቤ እንዳለበት ሰው ሲደባበቁን ኖረው ዛሬ ከሞቱ በኋላ ተሰናበቷቸው እየተባልን አበሳችንን ያየንበት ምክንያት ነው።

ያው ባለፈው ሰሞን ለማሳየት እንደሞከርኩት በርካታ መስሪያ ቤቶች እና ቀበሌዎች ህዝቡን በደብዳቤ አንዴ “እናሳስባለን” አንዴ “እናስጠነቅቃለን” እያሉ ሲያስለቅሱት ሰንብተዋል። ግን እኮ በፈቃዱ ያለ ቀስቃሽ ያለቀሰው ሰው በቂ ነበር። ኢህአዴግ ግን ሰው አይጠግብም። ብለን ካወደስነው በኋላ በተለይ ለማስለቀስ ሲሆን በርከት ሲል ደስታው ነው ብለን ሀቁን እንናገረለን!

ለማንኛውም አሁን የጠቅላይ ሚኒስትሩ ግባተመሬት ተፈፅሟል። አንዴ ዘቅዝቀው ሲይዙት አንድ ጊዜ ደግሞ “ጨርቅ ነው” እያሉ ሲያጣጥሉት የነበረው ባንዲራም አብሯቸው ተቀብሯል። ይሄ ታሪካዊ ስህተት ይመስለኛል። እንዲያ ያንጓጠጡት አንሶ ደግሞ አብሯቸው መቀበሩ በእውነቱ ተገቢ አይመስለኝም። (አረ እንደውም የምን አይመስለኝም ነው…!? ነውር ነው እንጂ!)

በነገራችን ላይ የጠቅላይ ሚኒስትሩ አስከሬን ወደፊት ደግሞ በስማቸው በሚገነባው ወመዘክር ውስጥ እንደሚቀመጥ ተነግሮናል። ስለዚህ አቶ መለስ “ግባተመሬት” እንደተባሉት ሁሉ ገና ደግሞ “ውጣተመሬት” አለባቸው ማለት ነው…! ወይ አበሳቸው! ግን የዚህስ ጠቀሜታ ምንድነው? እሺ ወመዘክሩ ይገንባላቸው። አስከሬናቸውን ግን በዛ ቦታ እናስቀምጣለን ብሎ ማለት ባለስልጣኖቻችን በስሜት እንጂ በስሌት እየመሩን እንዳልሆነ የሚያሳይ ይመስላል…!

ለማንኛውም አሁንም ከአስራ አምስቱ ቀናት “ብሔራዊ ሀዘን” በኋላም ጠቅላይ ሚኒስትሩን የሚያወድሱ የቴሌቪዥን ፕሮግራሞች አልተቋጩም። አሁንም አቶ መለስ ዜናዊ ተወዳጅ እና “ተመላኪ”  እንደነበሩ እየተነገረን ነው። መቼም አሁን ሞተዋልና እሺ ይሁንላቸው ተወዳጅ ነበሩ እንበል…! ግን ምን ይጠበስ…?

አሁንም አስከሬናቸው ይግዛን? ወይስ ምን እናድርግ…? ግራ ነው የሚያጋባው! አረ “ያልሞታችሁት” የኢህአዴግ ባለስልጣናት ቢያንስ ይቺን ቀሪ ሶስት አመት መንግስት መንግስት ምሰሉን…!

በደህናው መንገድ ምሩን እና “ተወዳጅ” ለመሆን እስቲ ዕድላችሁን ተጠቀሙ…! እንጂ በድሮው በሬ አትረሱ… በሬውም ይረፍበት!አቤቶክቻው

 

Happy
Happy
0 %
Sad
Sad
0 %
Excited
Excited
0 %
Sleepy
Sleepy
0 %
Angry
Angry
0 %
Surprise
Surprise
0 %
    Print       Email
  • Published: 12 years ago on September 3, 2012
  • By:
  • Last Modified: September 3, 2012 @ 6:58 pm
  • Filed Under: Ethiopia
  • Tagged With:

Average Rating

5 Star
0%
4 Star
0%
3 Star
0%
2 Star
0%
1 Star
0%
<"Without the support of our readers, the Maleda Times website would not exist in its present form">

You might also like...

በሰሜን ሸዋ ዞን ኤፍራታ እና ግድም ወረዳ መከላከያ ከአማራው ማህበረሰብ እና ከፋኖ ጋር ጦርነት ገጥሟል

Read More →

This site is protected by wp-copyrightpro.com

%d bloggers like this:
Skip to toolbar